Login
Main menu

ሆሣዕና

Index

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ሆሣዕና፡- በዚህ ዕለት ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ክብር ወደ ኢየሩሳሌም የገባበትን ቀን እናስባለን፡፡ በዓለ ሆሣዕና ከጌታችን ፱ቱ ዓበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ከሌሊት ጀምሮ በታላቅ መንፈሣዊ ሥርዓት ይከበራል፡፡ በሌሊቱና በዑደቱ ሥርዓት ላይ ብቻ ከዘጠኝ ያላነሱ ምስባኮች ስለሚደርሱ ሁሉን መተርጐምን ለጊዜው ታግሠን የትኞቹ እንደሆኑ እንድናውቅ ብቻ ማመላከቻ እንሰጣለን፡፡

ምስባክ፡-መዝ፹፥፫፤መዝ፻፲፯፥፳፮፤መዝ፻፳፩፥፩፤መዝ፻፵፯፥፩፤መዝ፻፲፯፥፳፯፤መዝ፱፥፲፩፤መዝ ፰፥፪፤መዝ፵፱፥፩፤መዝ፷፯፥፴፬

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ወደ ኢየሩሳሌም የገባበትን ሁኔታ አራቱም ወንጌላውያን ተባብረው ጽፈውታል፡፡ በማቴ 21፥1-17፤በማር11፥1-10፤ሉቃ19፥29-38፤በዮሐ12፥12-19 በመሆኑም አንዱ ወንጌላዊ የመዘገበውን ብቻ የጽሑፋችን መነሻ ከማድረግ ይልቅ ሁሉንም ወንጌላት መዳሰስን መርጠናል፡፡

ጌታችን ራሱን ለዓለም ገልጦ ማስተማር ከጀመረ ወደ ኢየሩሳሌም ሲወጣ ይኽ ለአራተኛ ጊዜ ነው፡፡ በዚሁም ጊዜ ቤዛነትን ፈጽሟል፡፡ ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም የገባው ከወትሮው በተለየ ሁኔታ ነው፡፡ በአህያናበውርንጫዋ ላይ ተቀምጦ፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈፀም ነው፡፡

ትንቢቱ “ለጽዮን ልጅ እነሆ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሉአት” ተብሎ ተጽፏል፡፡ ትን.ዘካ 9፥9

ምሳሌውም፡- በብሉይ ኪዳን ነቢያት ዘመነ ጸብዕ(ጦርነት) መምጣቱን ለማመልከት በፈረስ ተቀምጠው ዘገር ነጥቀው ይታዩ፤ ዘመነ ሰላም መምጣቱን ለማመልከት ደግሞ በአህያ ተቀምጠው መነሳንስ ይዘው ይታዩ ነበር፡፡ ጌታችን በዚህ ወደ ኢየሩሳሌም ለአራተኛ ጊዜ የመጣው በደሙ የጥልን ግድግዳ አፍርሶ በመካከላችን ፍፁም ሰላምን(ዕርቅን) ለማድረግ ነውና ይህንኑ ሲያመለክት ነው፡፡ በመከራዬ፣ደሜን በማፍሰሴ፣በስቅለቴ፣በሞቴ ሰላም የሚሆንላችሁ ጊዜ ቀርቧል ሲለን ነው፡፡

“ፈትታችሁ አምጡልኝ ለጌታ ያስፈልጉታል”

ደብረ ዘይት ቤተ ፋጌ ወደምትባል መንደር ሲደርስ ከደቀመዛሙርቱ ሁለቱን ሲልክ የሰጣቸው ትዕዛዝ ነው፡፡ የታሠሩ አህያና የአህያይቱን ግልገል ሲያገኙ የሚያደርጉትንና ለሚጠይቋቸው የሚሠጡት መልስ፡፡

ነባቢት ነፍስ ያለችው ሰውም ሆነ በደመ ነፍስ ሕያዋን የሆኑ ፍጥረታት መታሠርን አይወዱም፡፡ምክንያቱም በተፈጥሮ ያገኙትን የመንቀሳቀስ መብት ይፃረራልና ነው፡፡መታሠር ነፃነትን፣ መታሠር ፈቃድን ይጋፋል፡፡ እኒያ እንስሳት የታሠሩበት የራሱ ምክንያት ይኖራል፡፡ እንስሳት እንዳይጠፉ፣ሌባ እንዳይሠርቃቸው ወይም የሚያጠፉት ነገር ሲኖር እንዳይደርሱበት ለማድረግ ይታሠራሉ ወይም በሌላ አነጋገር ነፃነታቸው ይገደባል፡፡

ሰውንም እንደአስፈላጊነቱ ከጥፋት ለመጠበቅ በሕግና በደንቦች ይታሠራል፡፡ አስተዋይ የሆነ በኅሊና ህግ ይጠበቃል፡፡ እኒህን ሁሉ ያልተጠቀመባቸው በቦታ እንዲገደብ ያደረጋል፡፡በሰው ላይ በጫና ሳይሆን በስምምነት የሚወጡ አብዛኛዎቹ ሕጎች ነፃነቱን አይነጥቁትም፡፡ በኅሊናው ሕግ የሚመራ ግን በአፍአ ብቻ ሳይሆን በውስጥ ከሚኖርበት ሙግት ነፃ ስለሚሆን ፍፁም ሰላም ይኖረዋል፡፡ ከራሱ ከመሰሎቹ፣ከተፈጥሮና ከኒህ ሁሉ ገዢ ከልዑል እግዚአብሔር ጋር ህብረት፣ስምምነት፣ፍቅር፣አንድነት ይኖረዋል፡፡

ጌታችን ደቀመዛሙርቱን ሲልክ “ ፈታችሁ አምጡልኝ” ማለቱን መተርጉማን ሰው ሁሉ ከማዕሠረ ኃጢአት(ከኃጢአት ማሠርያ) የሚፈታበት ጊዜ እንደደረሠ ለማጠየቅ መሆኑን ይገልፃሉ፡፡ (ትርጓሜ ወንጌል ተመልከት)

ከእስራታቸው ተፈትተው ለጌታ ያስፈልጉታል እንደተባለ ጌታ ተቀመጠባቸው፡፡

- አዳምና ዘሩ ከሞት እስራት ነፃ ወጥተው የትንሣኤ ጌታ የሆነው የእርሱ ማደርያ ሆኑ፡፡

-አዳምና ዘሩ ሞትን ከሚያስከትል የሕግ እስራት ተለቀው፤ፍቅር ከዙፋኑ ስቦ ላወረደው አምላክ ዙፋን ሆኑ፡፡ በኦሪት የተሠጡን ትዕዛዛት ደገኛ ነበሩ፡፡ በማናቸውም ምክንያት እነዚያን ትዕዛዛት የሚተላለፍ ቢኖር ቅጣቱ በሞት ይፈፀማል፡፡ ይህም ሰውን ከሕጉ መልካምነት ይልቅ የቅጣቱን ክፋት እያሰበ በባርነት መንፈስ እንዲኖር አድርጎታል፡፡

ሰውም የእግዚአብሔርን አሳብ መረዳት ስላልቻለ ግንኙነታቸውን በፍርሃትና በሕግ ላይ የተመሠረተ አድርጎታል፡፡ ይህንን ሰብረው መውጣት የቻሉ እጅግ ጥቂቶች ብቻ ናቸው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን “ብትወዱኝስ ትዕዛዜን ጠብቁ” በማለት ሕጉን መተላለፍ በድንጋይ መወገርና በእሳት መቃጠልን ሳይሆን ከፍቅሩ መለየትን እንደሚያስከትል አስተማረ፡፡ አሁን ሕጉን የምንጠብቀው የሞት ቅጣትን በመፍራት ሳይሆን የአባታችንን ፍቅር ላለማጣት ነው፡፡ ሕጎቹ አልተሻሩም ቀድሞም ደገኛ ሕግ ነበሩና፡፡ ጌታችን ያሻሻለው እኛ ለሕግጋቱ ያለንን ግንዛቤ ነው፡፡ ሕጉን የምንፈፅምበትን መንፈስ ነው በውስጣችን ያደሰው፡፡ሕጉ በፍቅር ይጠብቀናል እኛም ሕጉን በፍቅር እንፈፅማለን፡፡ የአዲስ ኪዳን መንፈስ የወንጌል የምስራች ይኸው ነው፡፡ ዮሐ 14፥15፣ዮሐ15፥9-11 ሮሜ 7፥1-20

ዮሐንስ ወንጌላዊም በመልእክቱ “እግዚአብሔርን ስንወድ ትዕዛዛቱን ስናደርግ የእግዚአብሔርን ልጆች እንድንወድበዚህ እናውቃለን፡፡ ትእዛዛቱን ልንጠብቅ የእግዚአብሔር ፍቅር ይህ ነውና፡፡ ትእዛዛቱም ከባዶች አይደሉም” 1ዮሐ 5፥2-4

ፈታችሁ አምጡልኝ በማለቱ የእስር ሠንሰለታችን ተቆረጠ፡፡ ሞት በሰው ላይ የሠለጠነው ኃጢአትን ምክንያት አድርጎ ነበር፡፡ ዲያብሎስ ደግሞ ዓለምን የገዛው ኃጢአትንና ሞትን መውጊያው በማድረግ ነበር፡፡ ጌታችን የሰውን ሥጋ ተዋህዶ ኃጢአትን ባለመስራት ኃጢአትን፤ በሥጋ ሞቶ በመነሣት ሞትን፤በደመሰሰ ጊዜ የዲያብሎስ ግዛት ፈረሰ፡፡ ምክንያት የሚያደርግ ኃጢአትን ነበርና ጌታችን ግን “የዚህ ዓለም ገዢ ይመጣልና በእኔ ላይም አንዳች የለውም” በማለቱ የሰው ልጅ ለባርነት ምክንያት የሆነው የኃጢአት መርዝ እንደተወገዱለት አረጋገጠልን፡፡ ይህን የተናገረ ራሱን የሰው ልጅ ብሎ የሚጠራ ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና፡፡ ዮሐ14፥30፤1ቆሮ 15፥54-57

ይህ ብቻ ያይደለ በጸሎት በተመስጦ ከዚህ ዓለም ጭንቅና ፈተና፤በፆምና በተጋድሎ ከፍትወታትና ከእኩያት፤እውነትን በማወቅ ከወግና ከልማድ ትብታብ መፈታትን አደለን፡፡ ጥንትም ሰው የተፈጠረ በገዢነት መንፈስ እንጂ በተገዢነት ሁኔታ አልነበረም፡፡ሰው ሁሉን ይገዛል እርሱ የሚገዛው ግን ለልዑል እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ለእግዚአብሔር መገዛትም ነፃነት ነው፡፡  ለጌታ እግዚአብሔር ከመገዛት በራቅን ቁጥር ራሳችንን መግዛት አቃተንና ከእንስሳት እንኳ በግብር አንሰን እስክንታይ ተዋረድን፡፡ ሕግጋት ይመሩን ይደግፉን ዘንድ ቢሰጡንም ለመፈፀም አቅም አጣን፡፡ በመሆኑም ሕግጋቱ ኃጢአታችንን እየገለጡ እንደገና ዕዳ ሆኑብን፡፡ ቅ.ጳውሎስ “ነገር ግን በህግ ባይሆን ኃጢአትን ባለወቅሁም ነበር” እንዳለ ሮሜ 7፥9-10

ጌታችን ሰውነታችንን በወደዳትና በተዋሀዳት ጊዜ ከጸጋው ብዛት የተነሣ ከሕግ በላይ አደረግን፡፡ ከጌታችን ጋር ፍፁም ህብረት ያደረጉ ሁሉ ከሕግ በታች ሳይሆን ከጸጋው በታች ይሆኑ ዘንድ ተባለላቸው፡፡ በሕግ ቢኖሩም ሕግ እንዳለባቸው አያስቡም በጸጋው ይደነቃሉ እንጂ፡፡

ይህ ሁሉ ነፃ የመሆን የመፈታት ማሳያ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህን ሲያይ ነው “በነፃነት እንድንኖር ክርስቶስ ነፃ አወጣን” ያለው፡፡ ሮሜ 3፥21-31፤ሮሜ 6፥12-19፤ገላ 5-1

አስተውሉ “ፈትታችሁ ልቀቋቸው” አላለም “ፈትታችሁ አምጡልኝ፤ ማንም አንዳች ቢላችሁም ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ”አለ እንጂ፡፡ ከኃጢአት፣ከዓለም፣ከምኞት፣ከወግና ከልማድ ወዘተ…መፈታትን ወደርሱ ቀርበን ማደርያው ለመሆን ከእርሱ ጋር ለመሆን እንጂ ልንባዝን አይደለም፡፡

ወደ ሕይወታችን የተላኩ ካህናት ከእስራት የመፍታት ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል፡፡የሚፈቱን ወደ ጌታችን ለማቅረብ ነው፡፡ ከጌታችን ጋር የምንዋሃደውም ቅዱስ ሥጋውንና ክብሩ ደሙን በመቀበል ነው፡፡ ማንም በራሱ ሥልጣን ከኃጢአት እስራት መፈታት አይችልም፡፡ በራሴ ወደ ጌታ እቀርባለሁ በማለት የድፍረት ቃል መናገርም የተገባ አይደለም፡፡ እነሆ ሂዱ በማለት የሚፈቱንን የመንግስቱን ካህናት ልኳል፡፡ እነርሱም ከኃጢአት የምንፈታበትን ትምህርት ሥርዓት ጸሎትና ሥልጣን ይዘው እንፈታ ዘንድ ይጋብዙናል፡፡ ለምን? ለሚል መልሳቸው ለጌታ ታስፈልጉታላችሁ! ነው፡፡ ማቴ 18፥18፤ዮሐ 20፥23

ሰው ሆይ የተሰጠህን ክብር ተመልከት፡፡ ፍጡር ሳይኖር በፈጣሪነቱ፤ተገዢ ሳይኖር በአምላክነቱ፣ አመስጋኝ ሳይኖር በአኰቴቱቅድመ ዓለም ነግሦ ለሚኖር፤እልፍ አእላፋት ወትልፊት አእላፋት መላእክት፤የሚታየውና  የማይታየው ሁሉ ለሚገዛለት ለእርሱ ታስፈልጉታላችሁ መባላችን እንዴት ያለ ክብር ነው?፡፡ ፈጣሪነቱ በእኛ ታወቀ አንል ከእኛ ይልቅ ብዙ ፍጥረት ተዘርግቷል፤ያለእኛ ተገዢነት ጌትነቱ አይሟላም እንዳንል ሳንፈጠርም በጌትነቱ ኑሯል፤ ታዲያ “ለጌታ ያስፈልጉታል”መባላችን ስለ ምንድር ነው?/ቅዳሴ ዲዮስቆርስ/


More in this category: « ኒቆዲሞስ ስቅለት »

Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ