ዐቢይ ፆም
Featured
፩.ዘወረደ፡- በሌላ ስሙ ፆመ ሕርቃል በማለት ይታወቃል፡፡ ንጉሥ ሕርቃል/Heraklis/ በፋርስ ንጉሥ መከራ የፀናባቸውን ክርስቲያኖች ነፃ ለማውጣት ሲዘምት በፆም በጸሎት እንዲያስቡት በመጠየቁና ዘመቻውም በስኬት ሰለተጠናቀቀ ያን ለማዘከር ይፆማል፡፡
በዋናነት ግን ዘወረደ በተባለው ሳምንት የምናስበው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ከሰማያት መውረድና በሥጋ መገለጥ ነው፡፡ በዚህ ዕለት የሚሰበከው ምስባክና የሚነበበው ወንጌል እንደሚከተለው ነው፡፡
ምስባክ፡- ተቀነዩ ለእግዚአብሔር በፍርሃት
ወተሐሰዩ ሎቱ በረዓድ
አፅንዕዋ ለጥበብ ከመ ኢይትመዓዕ እግዚአብሐር መዝ ፪፥፲፩
ምክር፡- ነቢዩ ዳዊት በመንፈስ ቅዱስ የመከረን ታላቅ ምስጢር ነው፡፡ ”ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ” አለ የተገባ ነውና፡፡ በሌላው ዝርዝር ሳንገባ የመግደልም ሆነ የማዳን ፈርዶ ሲዖል የማውረድም ሆነ ይቅር ብሎ ለዘላለም ደስ ማሰኘት የልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ነው፡፡ እኔ እገድላለሁ አድንማለሁ፤እቀስፋለሁም ይቅርም እላለሁ ከእጄ የሚያድን የለም ጨምሮም እርሱን ፍሩት ነፍስንና ሥጋን አንድ አድርጎ በገሃነም ሊያጠፉ የሚችለውን ተብሎ ተጽፏል፡፡ ዘዳ 32፥39፣ማቴ 10፥28
ፍርሃት የልቡና ድንጋፄ የናላ ረዓድ የጉልበት ነው፡፡ ለጌታ እግዚአብሔር በፍርሃትና በረዓድ ሆናችሁ በመገዛታችሁ ደስ ይበላችሁ፡፡ አንድም ኃይል ከጉልበት ጋር የተያያዘ እንደመሆኑ በፆም በጸሎት በስግደት በውስጥ(በልብ) በአፍአ(በጉልበት) እየተገዛችሁ ኃይል ሥጋዊን በማድከማችሁ ደስ ይበላችሁ እርሱ ኃይል መንፈሳዊን ያድላችኋልና፡፡ “ኃይሌ በድካም ይፈፀማልና” ጸጋዬ ይበቃሃል እንዲል፡፡ 2ቆሮ12፥9
የጌታ እግዚአብሔር ቁጣ በላያችሁ እንዳይሆን ጥበብ መንፈሳዊን አጽንታችሁ ያዙ፡፡ ጥበብ መንፈሣዊ የተባለውም ፈሪሃ እግዚአብሔር፣አምልኮ ሠናይ፣ጸሊዓ እኩይ፣ተፋቅሮ፣ትህትና ጾም ጸሎት ምፅዋት ወዘተ… እና ከከርሠ መጻሕፍት ከከናፍረ ሊቃውንት የሚገኝ ምክር ሁሉ ነው፡፡ አንድም ጥበብ የተባለ ጌታችን ነው፡፡ አጽንታችሁ ያዙ አለ በእርሱ ማመንን ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ መምጣቱንና እርሱ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ መሆኑን የማያምን ሁሉ ከእግዚአብሔር ፍርድ አያመልጥም፡፡ በአድስ ኪዳን ታላቁ ኃጢአት በእግዚአብሔር ልጅ አለማመን ነው፡፡ ዩሐ 3፥16-21 ፣ ዩሐ16፥7-11፣1ዩሐ 5፥10-12፣ 1ዩሐ4-2 ተመልከት በእርሱ ማመን ማለትም ወረደ ተወለደ ተሰቀለ ሞተ ተነሣ ዐረገ ዳግም ይመጣል ብቻ ብሎ መናገር ሳይሆን ለምን ወረደ? ተወለደ? ለማንስ ተሰቅሎ ሞተ? በትንሣኤውስ ምን አገኘን? እኔስ የትንሣኤው በርሃን(ድል) ተካፈይ ነኝ ወይ? ወዘተ----እያሉ በውሳጣዊ ህሊና በማስተንተን በህይወት መግለጥ ነው፡፡ ይህ ሁሉ በእኛ ህይወት ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ካላመጣ ስመን ብቻ ክርስቲያን ተብሎ መሸከም ከፍርድ አያስጥልም፡፡
የሚነበበው ወንጌል ዩሐ 3፥10-24
በዚህ ምንባብ ውስጥ ያለውን ተዝቆ የማያልቅ ምስጢር ለጊዜው ታግሠን በሁለት ነጥቦች ላይ እናተኩር፡፡
፩. የሰማያዊው ልደት ምሥጢር ምስክርነት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስም ሆነ በስሙ ያመንን የእኛ ሰማያዊ ልደት ምሥጢር የተገለጠው በጌታችን ምድራዊ ልደት ነው፡፡ እርሱ ድኅረ ዓለም ከእመቤታችን ያለ አባት ተወልዶ ቅድም ዓለም ያለእናት ከአብ የተወለደውን ሰማያዊ ልደት ገለፅልን፡፡ ጌታችን በኒቆዲሞስ በተናገረው ቃል ላይ “ስለምድራዊ ነገር ስነግራችሁ ያለመናችሁ ስለሰማያዊው ብነግራችሁ እንዴት ታምናለችሁ? ሲል ምድራውያን ስለሆናችሁ ስለእናንተ ሰማያዊ ልደት ስነግራችሁ ያለመናችሁ ከዓለም አስቀድሞ ስለሆነ ስለእኔ ልደት ብነግራችሁ እንዴት ታምናለችሁ ሲል ነው? አንድም ሰለምድራዊ ልደቴ ስነግራችሁ ካለመናችሁ ስለሰማያዊው ብነግራችሁ እንዴት ታምናለችሁ? ሲል ነው፡፡
ሰማያዊውን ምሥጢር ሊገልጥ የተገለጠ ብቸኛው ከሰማይ የወረደው በሰማይም ያለው እርሱ ነው፡፡ በዚህ ቃሉም በሥጋ ቢወሰንም ምሉዕ ሰፋሕ ከመሆን እንዳልተለወጠ አስረዳ ምስክርነቱ ግን አልታመነም፡፡ ኢሳያስም“ ምስክርነታችንን ማን አመነ?“ ብሎ ተናግሯል፡፡ ይህም ቢሆን ግን ያየነውንና የሰማነውን እውነት መመስከር ግድ ነው፡፡ ይኸውም ህይወት ተገለጠ ዓይተንማል ሰምተንማል ሕይወት እንዲበዛላችሁ በእርሱ ፍቅር ኑሩ ብሎ መመስከር ነው፡፡ በምስክርነታችን በሰዎች ዘንድ አክራሪ፣ ሥራ ፈት ወይም ሌላ እነደሆንን ተቆጥረን መላገጃ ልንሆን እንችላለን፡፡ ክብራችንም ይኸው ነው፡፡
፪.የእግዚአብሔር ፈቃድ በልጁ መገለጥ:- የጌታ እግዚአብሔር የዘመናት ዕቅድ ሁሉ ይድኑ የክብሩም ወራሾች ይሆኑ ዘንድ ነው፡፡ ይህም በአንድያ ልጁ ሞት ተረጋገጠ፡፡ ይህን ፍቅር ለመግለጥ ልብ ይደክማል፣አእምሮ በአንከሮ የሸነፋል፣አንደበት በዝምታ ይታሠራል፣ቃለትም ይፈራሉ፡፡ የባርባሮስ ጥልቀት የሰማያትም ምጥቀት የረቂቁም ሆነ የግዙፉ ዓለም ስፋት ይህን ፍቅር ሊሸከመው ሊገልፀው አይችልም ምትክ ከሌለው ልጅ በላይ ጠላትን መውደድ በአብ ዘንድ፤ከራስ በላይ ጠላትን መውደድ በልጁ ዘንድ ምን ይደንቅ? በወንጀለኛ ተገብቶ ካሣ ሞትን ወስዶ ህይወትን ማደል እኔም በአባቶቼ መንፈስ ጌታ ሆይ እጠይቅሃለው ታስበው ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ከሌሎች ይልቅ እስከዚህ ትደርስለት ዘንድ ሰው የመሆን ምሥጢር ምንድር ነው?
*በዘወረደ በትህትና ወርደን በመንፈስ መጥቀን የምናስበው ይሔን ነው!
2 comments
-
My cofession Father Kal Hiwot yasemalen my comment is there are some error letters and words due to type error next I expect the 5th week