ዐቢይ ፆም
Featuredበስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!
እስከ ቅርቡ ጽሑፍ አነሣው የነበረውን አሳብ ተግ አድርጌ፤አዲስ የምጽፈውንም ሚያዝያ እስኪብት አቆይቼ በያዝነው የፆም ጉዳይ ላይ ልጽፍላችሁ መልካም መስሎ ታየኝ፡፡
በቀኖና ቤተክርስቲያን ከተደነገጉት ዓበይት አፅዋማት አንዱ ፆመ ኢየሱስ (ዐቢይ ፆም ወይም ሁዳዴ) አንዱ ነው፡፡ ጌታ ስለፆመው ፆመ ኢየሱስ ወይም ዐብይ ፆም፤ ሁሉ ተስተካክሎ ስለሚፆመውም “ሁዳዴ” ተብሏል፡፡ የሁዳድ እርሻን ሁሉ በህብረት እንዲሰራው በዚሁ አንፃር ነው፡፡
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እፀድቅ አይል ጻድቅ፣ እቀደስ አይል ቅዱስ፣እነፃ አይል ንፁህ፣ ኃይል መንፈሳዊ አገኝ አይል ኃይል የባህርዩ የሆነ፣ ከኃጢአት ሥርየት ለማግኘት አይል “የዓለምን ኃጢአት የሚያስተሠርይ የእግዚአብሔር በግ” የተባለለት መስተሥርዬ ኃጢአት፣ፍትወታት እኩያትን አስታግስ አይል ከድቀት በፊት የነበረ የቀዳማዊውን አዳም ክብር ይመልስ ዘንድ የተገለጠ ዳግማዊ አዳም ስለምን ፆመ? ቢሉ መልሱ እንዲህ ነው፡፡
ጌታ ሥጋን ተዋህዶ በዚህ ምድር ሳለ የሠራውን ሁሉ ሰለ ዐራት ምክንያት አድርጎታል፡፡
፩. ለቤዛ(ለካሣ) ዓለም
፪.ለአጽድቆተ ትስብዕት( ፍፁም ሰው መሆኑን ለማጠየቅ)
፫.ለአቅርቦተ ሰይጣን(ሰይጣን አቅርቦ ለማሠር)
፬. ለአርአያነት ነው፡፡
ሦስቱን ጊዜ በፈቀደ እስኪገልጣቸው የፆሙን እንመልከት ተያያዥነቱ ከአራተኛው ጋር ነውና፡፡
፩. ጌታ የፆመው “ለአርአያነት” ነው፡፡ ፈጽሞ ቅሉ “ከመዝ ግበሩ”(እንዲህ አድርጉ)” ማለት የተመቸ ነውና፡፡ መልካም መምህር ተናግሮ ማስረዳት ፈፅሞ ማሳየት አርአያ ትቶ መምራት መገለጫው ነውና፡፡ ከዚህ የወጣ መምርነት የለም፡፡ በአፍ ብቻ ቢለፈልፉ ኪያስፈርድ በቀር ረብ ጥቅም አይገኝበትም፡፡ ስለጌታችን ግን ቅዱስ ጴጥሮስ “የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሏልና” ሲል ገልፆታል፡፡ ይህም ጹሞ ጹሙ፣ጸልዮ ጸልዩ፣ ታግሦ ታገሡ፣ አፍቅሮ ተፋቀሩ… ወዘተ፡ ማለቱ አይደለምን? 1ጴጥ 2፥21
፪. ጌታችን የመጣ ኦሪትንና ነቢያትን ሊፈፅም ነውና ትንቢታቸውን ፈጽሞ ኑሯቸውን ኑሮ የነቢያቱን እውነተኛነት አተመ፡፡ ክቡደ መዝራዕት ሙሴ በሲና ኤልያስም በቀርሜሎስ ሌሎችም ዓበይትና ደቂቀ ነቢያት ፆምን አብዝተው ይፆሙ ነበርና “ተቸግረው ወይንም የማያስበላና የማያስጠጣ ጋኔን አድሮባቸው ሳይሆን ከፈጣሪያቸው ኃይል መንፈሳዊን የተቀበሉበት አምላካዊ ምስጢራትን ያዩበት ረቂቀ መንገድ መሆኑን ለማስረገጥ ጌታም ፆሞታል፡፡ በዚህም የነቢያቱን ፆማቸውን አተመ መንገዳቸውንም አፀደቀ፡፡ ማቴ 5፥17 ማቴ 11፥18
፫. አጋንንትን ፍትወታት እኩያትን ድል የምንነሣበትን ኃይል መንፈሣዊ እንዴት እንድናገኝ ሲያመለክተን ፆመ ፡፡ ጌታን በፆሙ ወቅት ዲያቢሎስ በስስት ቢመጣበት በትዕግስት፣በፍቅረ ነዋይ ቢመጣበት በጸሊዓ ነዋይ፣ በትዕቢት ቢመጣበት በትህትና ድል ነስቶታል፡፡ በዚህም ከዲያቢሎስም ሆነ ከባህርያችን የሚመጡብንን ፈተናዎች እንዴት ባለ መንፈሳዊ ጥበብ እንደምናሸነፍ ገልፆልናል መንፈሳዊው ትጥቅና የጦር አሠላለፍ መልኩ ይህ ነው፡፡ በድካም ውስጥ ያለ ኃይል፡፡ ጥበብ በዚህ አለ ልብ ያለው ልብ ይበል! 2ቆሮ 10፥2-5
፬. መምራችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፆሙን በምድረ በዳ አደረገው፡፡ ይህም ህሊናችንን ከምግብና ከመጠጥ በሥጋ ከሚሆንም ተድላ ደስታ ሀሳብ ሁሉ ለዩት ሲለን ነው፡፡ መዓዛ መባልዕቱን በአጼንዎ ህሊና እያሸተቱ ፤ የማዕዱን ዓይነት በዓይነ ህሊና እየላሱ መፆም “ቁጭት” እንደሆን እንጂ ፆም አይሆንም፡፡ በፆም የምንማረው አምላካዊ ታላቅ ምሥጢር “ሰው በእንጀራ ብቻ እንደማይኖር” ነውና፡፡ በዚህ ወቅት ሰውነት(ነፍስና ሥጋ) ከመብል ከመጠጥ ርቆ በመንፈስ ሠረገላ መጥቆ የእግዚአብሔር መንግሥቱንና ጽድቁን በመመኘት ሀሴት ያደርጋል፡፡ ጊዜው ላመሉ ሲደርስ ለቁመተ ሥጋ ያህል ያለ ሀሳብ ብዛት ያስተናግዱታል፡፡ ስለ እንጀራ ብቻ የሚያስብ ከዲያቢሎስ ስለፆም፣ ስለጸሎት ስለተጋድሎ የሚያስብ ከክርስቶስ መሆኑ በገዳመ ቆሮንቶስ ተለይቷል፡፡
ጌታችን ምድረ በዳውን ለመናንያን ባርኮ ሠጣቸው ይህ ባይሆን ቅሉ ምድራውያን መላእክት የበረሃ ከዋክብት የተባሉ አበው ባልተገኙም ነበር፡፡ እነርሱም በዓለም ያለ መብል መጠጥ ሹመት ባለጠግነት ሳያምራቸው በፆም በጸሎት ጽሙዳን ሆነው ባለቤቱን እርሱን መስለው ኖሩ በመንግስቱም ባለሟሎች ይሆኑ ዘንድ ተገባቸው፡፡
እንስሳትም ሆኑ አራዊት ከተወለዱባት ደቂቃ ጀምረው የሚያስቡ ስለ ምግባቸው(ሆዳቸው) ነው፡፡ ያለፈ ታሪክ አይጠይቁም ከእነርሱ በፊት የነበሩት በምን ተጠቀሙ በምንስ ተጎዱ ብለው አይመረምሩም፡፡ ለወደፊትም ፈጣሪያችን የሚደሠትበት የበጀ ሥራ እንሥራ ብለው አይጨነቁም፡፡ እንግዲህ ሰውም ነጋ ጠባ ስለሆዱ ብቻ የሚያስብ ከሆነና ያለፈን መርምሮ ለወደፊቱ ተምሮ የማይኖር ከሆነ ከእንስሳት በምን ይለያል? ልጆቹም በምግበ ሥጋ ብቻ የሚያሳድግ ቤተሰብ ሥራው እንስሳት ከማርባት በምን ይሻላል?
ወደ ሕይወት መድኃኒት እንቀርብበት ዘንድ ቀድሶ የሠጠንን ፆም እንደተለመደው ያይደለ እንደሚገባው ፆመን ዋጋ የምናገኝበት ያደርግልን ዘንድ ቅዱስ ፍቃዱን ደጅ እየጠናን በዐቢይ ፆም ውስጥ ሰለምናሳልፋቸው(ሰለምናከብራቸው) ሰንበታት በድርበቡ እንመልከት፡፡
በዓቢይ ፆም ውስጥ የሚገኙ ተሰዓቱ ሰንበታት የተለያየ ስያሜ አላቸው፡፡ የመጀመሪያው...
2 comments
-
ውድ ዘክርስቶስ
ስለ ገንቢው አሰተያየትህ የድህረ ገጹ አስተባባሪዎች ያመሰግናሉ፡፡
ስለነበሩት የፊደላት ግድፈትም መላውን አንባቢ ይቅርታ እየጠየቅን አሁን ታርመው መውጣታቸውን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ ሆኖም ግን አሁንም የተዘለሉ ካሉ ጥቆማችሁን በደስታ እንቀበላለን
Web admin -
My cofession Father Kal Hiwot yasemalen my comment is there are some error letters and words due to type error next I expect the 5th week