Login
Main menu

Items filtered by date: June 2026

“መንሹ በእጁ ነው፤ ...... "

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!

“መንሹ በእጁ ነው፤ አውድማውን ያጠራዋል”   ማቴ 3:12

በምህረቱ ባለጠጋ የሆነ ጌታ እግዚአብሔር የመጨረሻውን ፍርዱን ከመግለጡ በፊት የንስሐ ዕድል መስጠት ልማዱ ነው፡፡ ይህንን እውነታ ከኖኅና ከሰዶም ሰዎች ገጠመኝ ከነነዌም ታሪክ በግልጽ ማየት ይቻላል፡፡ የተመለሱ ድነዋል፤ በልባቸው ጥንካሬ ጸንተው በክፋት የቀጠሉ ጠፍተዋል፡፡ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ከላይ የተጠቀሱትን ታሪኮች እንደማሳያ ተጠቅሞባቸዋል፡፡ የሰማው የለም እንጂ፡፡ ማቴ 12፡41፤ ማቴ 24፡38፤ ሉቃ 17፡28-32

አውድማውን ያጠራ ዘንድ መንሹን የያዘው ከመገለጡ በፊት ቤተ አይሁድ በክፋት ላይ ክፋት እየጨመሩ ሄደው ነበር፡፡ ዕለት ተዕለት ጌታ እግዚአብሔርን በከንፈራቸው ምህረትንና በረከትን በሥራቸው ግን ፍርድንና ጥፋትን እየለመኑት ነበር፡፡ ሁሉን ቻይ የሆነው እርሱ ግን አባቱን በግፍ ያስገደሉበትን ብላቴና ለበቀል ሳይሆን ወደ ምህረት ጮኾ እንዲጠራቸው ላከው፡፡ በምድረ በዳ (አበው በትርጓሜ ምድረ በዳ የተባለ የአይሁድ ልቡን ነው፡፡ ምድረ በዳ ውሃ ልምላሜ እንደሌለበት የአይሁድ ልቡናም ከሃይማኖት ከምግባር የተራቆተ ነበር ይላሉ፡፡ ስም፣ ሥርዓትና ምልክት ብቻ ቀርቶላቸው ነበር፡፡ ዛሬም በእኛ ዘንድ ያለው ክርስትና ስም፣ ሥርዓትና ምልክት ብቻ ቀርቶልን በፍቅር ከሆን ሃይማኖትና ምግባር ጠፍ ሆነናል) የተገለጠው ሰባኪም በትምህርቱ የነበሩበትን ሁኔታ ገልጦ አሳያቸው፡፡ ትምህርት መስታወት ነው፡፡ መስታወት ፊታችን ላይ ያለብንን አደፍ ጉድፍ ገልጦ ቢያሳይ እንጂ እንዳያፀዳ ትምህርትም በራሱ ድኅነት አያመጣም፤ ነውርን ገልጦ ያሳያል እንጂ፡፡ ሰምቶ መመለስ ለእያንዳንዱ የተተወ ምርጫ ነው፡፡ ትምህርቱም በሦስቱ መደብ ተለይቶ የቀረበ ነበር፡፡ ለቤተ ክህነቱ፣ በመንግሥት አስተዳደር ለነበሩና ለሕዝቡ፡፡

ከሕዝቡ እንጀምርና በደረጃ ወደ ላይ እየወጣን ለመመልከት እንሞክር፡፡ ሕዝቡ የዮሐንስን ትምህርት ሰምተው ምን እናድርግ? ሲሉ የመከራቸው “ሁለት ልብስ ያለው አንዱን ለሌለው ይስጥ፤ ምግብም ያለው እንዲሁ ያካፍል” በማለት ነው፡፡ በዚህ ንግግሩ ሕዝቡ የነበረበትን ሁኔታ ገልጾታል፡፡ ሰው ከመረዳዳትና ከመተዛዘን ይልቅ ሁሉ በግለኝነት መንፈስ የሰከረበት፤ ሀብት በማከማቸት የታወረበት፤ ለወገን መራራት እንደ ሞኝነት የተቆጠረበት፤ ተካፍሎ መብላት በነበር የቀረበት፤ በልጦ መታየትና በወንድም ላይ መኩራት መለያ የሆነበት ዘመነ እኪት ነበር፡፡ ቤተ አይሁድ የኖሩበት የአባቶቻቸው ባህል ይኸውም መተዛዘን፣ መረዳዳት፣ መተባበር ከመካከላቸው ጠፍቶ በምትኩ በተደጋጋሚ በባርነት የገዟቸው የአህዛብ ልማድ አማሰናቸው፡

፡ በይበልጥ የሄለናውያን(Helenistic) የአመለካከትና የአኗኗር ዘይቤ ከፍተኛ ተጽዕኖ የማንነት ግራ መጋባት ትግል ውስጥ ዘፈቃቸው፡፡ የጥንቱን የአይሁድ ባህል እንዳይጠፋ በሚቀኑና በአዲሱ ልማደ አህዛብ በተጠመቁ መካከል ልዩነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ ይሰፋ ነበር፡፡ ይህም በአንድ አሳብ ተስማምቶና ተረዳድቶ ከመኖር ይልቅ በልዩነት ለመነታረክ ምክንያት ሆነ፡፡ እንኳን በጠላቶቻቸው ላይ ድል ሊያገኙ ቀርቶ እርስ በርሳቸው በጠላትነት አንዱ በሌላው ላይ ተነሱ፡፡ ዛሬ በእኛም የሚታይ ቤተ አይሁድ ጥፋታቸው በቀረበበት ጊዜ ያሳዩ የነበረው ጠባይ ነው፡፡ ቀድሞ እንታወቅባቸው የነበሩ አባቶቻችን በሰላምና በበረከት እንዲኖሩ ያስቻሏቸው አብሮ በመተሳሰብና በመተዛዘን መኖር ከእኛ ርቋል፡፡ ከስግብግብነታችን ብዛት አማራጭ በማይቀርብላቸው የጤናና የትምህርት ጉዳይ ላይ እንኳ ወገናችንን እንዘርፋለን፡፡ በሰው ጤናና ነገ ሀገር በሚረከቡ ሕጻናት ሕይወት ላይ ከመነገድ የከፋ ኅሊና ቢስነትና የሥነ ምግባር ዝቅጠት የለም፡፡ ኢትዮጵያውያን አሁን ባለንበት ማንነት ዓይናችንን ቀና አድርገን ከጌታ እግዚአብሔር ዘንድ ምህረትንና በበረከት የተሞሉ ዘመናትን ለመለመን የሚያበቃ የሞራል ብቃት የለንም፡

፡ ምህረት የሚሰጠው በራሳቸው ላይ ሊደረግባቸው የማይወዱትን በሌላው ላይ ለማያደርጉና ምህረት ለተገባቸው ነው፡፡ ለግፈኛ ምህረት ማድረግ በክፉ ሥራህ ግፋበት እንደማለት ነው፡፡ አሁን የሚያድነን ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት ወዘተ .

. . አይደለም፤ ግፍ መሥራትን ማቆም እንጂ፡፡ ግፍ እየሠሩ ጾምና ጸሎት በጌታ እግዚአብሔር ላይ መዘበት ነው፡፡

በሀገር አስተዳደር ረገድ ደግሞ የሮም መንግሥት ሕግንና የሠለጠነ የአስተዳደር ዘይቤን ሽፋን በማድረግ ብዙ ግፍ ይፈፅም ነበር፡፡ ዛሬ ብዙ በኢኮኖሚ ራሳቸውን ያልቻሉ የዓለም ሀገራትን በዲሞክራሲና በሰብዐዊ መብት ሽፋን ሴራን እየደበቁ የማድቀቅና የማንነት ክስረት ውስጥ የመክተት አካሄድ ዛሬ የመጣ ሳይሆን ከቀድሞ የተወረሰ ነው፡፡ ዛሬም እኛ በግልፅና በሥውር ማን እንደሚገዛን የታወቀ ነው፡፡ ዛሬ ያሉ መንግሥታት ታላላቅ ግፍ የሚፈጽሙ የሕገ መንግሥትን፣ የዲሞክራሲንና የሰብዓዊ መብቶችን ድንጋጌ ጭምብል አጥልቀው ነው፡፡ እንዲህ ያሉትን ክቡር ዳዊት በመንፈሰ ትንቢት ተመርቶ እንዲህ ገልጿቸዋል፡፡

ሰነፍ በልቡ አምላክ የለም ይላል፤

በሥራቸው ረከሱ ጎሰቆሉ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ የሚያስተውል እግዚአብሔርንም የሚፈልግ እንዳለ ያይ   ዘንድ፤

 



እግዚአብሔር ከሰማይ የሰው ልጆችን ተመለከተ፤ ሁሉ ዓመፁ በአንድነትም ረከሱ፤

በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ የለም፤ ጉሮሮአቸው የተከፈተ መቃብር ነው በምላሳቸው ሸነገሉ፤ ከከንፈራቸው በታች የእባብ መርዝ አለ፤

አፋቸው መርገምንና መራራን ተሞልቷል፤ ደምን ለማፍሰስ እግራቸው ፈጣን ነው፤ ጥፋትና ጉስቁልና በመንገዳቸው አለ፤ የሰላምን መንገድ አላወቁአትምና፤

እግዚአብሔርን መፍራት በዓይናቸው ፊት የለም፡፡

በኢትዮጵያም ዛሬ በዲሞክራሲና በሰብዓዊ መብት ሽፋን ለእውነት በቆሙ ላይ ብዙ ግፍ ይፈጸማል፡፡ አንድ ሀገር ሕግ ካለው ሕግን ማክበር ያለበት ሕዝቡ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ እኛ ባሥልጣናት አረዳድ ግን የእነርሱ ግዴታ ሕግን ማስከበር እንጂ ሕግ ማክበር አይደለም፡፡ የመንግሥት ሹመኞች በየደረጃቸውና እንደየአቅማቸው ሕግን ሲጥሱ ጠያቂ የለባቸውም፡፡ ለመጠየቅ የግድ ከሥልጣናቸው መውረድ አለባቸው፡፡ ተጠያቂነትን ስለሚፈሩትና ውጤቱንም ስለሚያውቁ ሥልጣን ለእነርሱ ሕዝብ ማገልገያ ሳይሆን የደኅንነታቸው ዋስትና ነው፡፡ በሁሉ ላይ የሠለጠነው እውነተኛው ፈራጅ አውድማውን ሊያጠራ በፍርድ ሲገለጥ ግን ሕጋችሁም፣ ሥልጣናችሁም ሆነ የሽንገላ አንደበታችሁ መደበቂያ አይሆኗችሁም፡፡ ልዑሉ ምን ሊያደርግ እንደሚችል ፈርዖንንና ናቡከደነፆርን አልጠቅስም፡፡ ትናንት አጠገባችሁ የነበሩና ዛሬ የሌሉትን ማየት በቂ ነው፡፡ ማየት ከቻላችሁ!!! እያንዳንዱ ሸፍጥ ግፍ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ነገ በሌላው ይቅርና በራሳችሁ ልጆችና የልጅ ልጆች ሳይቀር የተናቃችሁ፣ የተጠላችሁና የምትረገሙ ትሆናላችሁ፡፡ ነገ መልስ መስጠት ለሕሊናዬ ነው የምሠራው ብላችሁ እንደ መመፃደቅ ቀላል አይሆንም፡፡ ኢትዮጵያን ያደቀቀው ሕዝቡን የደኅንነት ሥጋት ላይ የጣለውና እግዚአብሔርም የተፀየፈው ባልተገራ ኅሊናችሁ ላይ መደገፋችሁን ነው፡፡

በቤተ አይሁድ በመንግሥት አስተዳደር መዋቅር ላይ የተቀመጡትም ሠርቶ ለማደር ደፋ ቀና የሚለውን ለፍቶ አደር ከተፈቀደው በላይ ቀረጥ እየጫኑ ያስጨንቁት ነበር፡፡ በዚህም ነው ዮሐንስ ቀራጮችን “ከተፈቀደላችሁ አብልጣችሁ አትውሰዱ” ሲል የገሰፃቸው፡፡ በኢትዮጵያ እየተፈጸመ ያለው ግን ለመናገር የሚያስጨንቅ ነው፡፡ በመጽሐፍ “ሕዝቤን እንደ እንጀራ የሚበሉ አያውቁምን?” ተብሎ እንደ ተጻፈ በዚህ የከበሩ ሁሉ በቁም ሳሉ ጭንቀትና ደዌ ሲሞቱ ደግሞ የእግዚአብሔር ፍርድ የሚበላቸው ናቸው፡፡ ቢፈጥንም ወይ ቢዘገይም በችግር ከደረቀ ሰውነቱ የሚወጣ የደሃ ዕንባ መልስ ማግኘቱ አይቀርም፡፡

ሕዝብ ለመጠበቅ ቃል ኪዳን የፈጸሙ ወታደሮችም የደመወዛቸውን ማነስ ለማካካስ ሰውን መማለጃ ለመቀበል በሀሰት እየከሰሱ ያስጨንቁ ነበር፡፡ የታመነው ሰባኪ ጭፍሮች ሲጠይቁት “በማንም ላይ ግፍ አትሥሩ፤ ማንንም በሀሰት አትክሰሱ፤ ደመወዛችሁም ይብቃችሁ” በማለት ያለ ፍርሃት በደላቸውን ነግሯቸዋል፡፡ በሀገራችን የሕግ መከበር የሌለው ሕግ ስለ ሌለ ሳይሆን ሕግ አስፈጻሚ አካላት በተለያየ ምክንያት (ሙስና፣ ዘር፣ ሃይማኖት፣ ቡድን፣ የፖለቲካ አመለካከት፣ ወዘተ .

. .) ስለሚሸረሽሩት ነው፡፡ ብልሹ ሕግ አስፈጻሚዎች ባሉበት እንኳን የሰዎችን ቀርቶ ፍፁም ንፁህ የሆነውን ሕገ እግዚአብሔርን ማስፈጸም እጅግ ከባድ ነው፡፡

ከላይ የተጠቀሱትን ሁሉ መምከር፣ መገሠፅና ማስተካከል ያለበት የቤተ ክህነቱም በተመሳሳይ ነቅዞ ነበር፡፡ ሥርዓት ደንጋጊና ሕግ አስፈፃሚ የሆነ አካል ራሱ የእግዚአብሔርን ሕግ ከናቀ የጥፋት ሥር ይሆናል፡፡ ከውድቀት (ከጥፋት) በፊት በአይሁድ መካከል የታየ የመጀመሪያ ምልክት ከፍተኛ የሆነ መከፋፈል ነበር፡፡ ፈሪሳውያን፣ ሰዱቃውያን፣ ኤሴያዊያን፣ ቀነናውያን ወዘተ . . . ተብለው በቡድን ተከፋፍለዋል፡፡ አንዱ ከአንዱ ጋር አይተባበርም ነበር፡፡ ኢትዮጵያንና ቤተ ክርስቲያንንም ይኸው የመከፋፈል ምች የመለያየት ዋግ መቷቸዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ”አይሁዳዊ ግሪካዊ የለም ሴት ወንድ ጌታ ሎሌ የለም ሁሉ በክርስቶስ አንድ ሆኗል” የሚለው ተረስቶ በዘር መሳሳብ ሰልጥኖብና፡፡ መከፋፈል መለያየት ደግሞ የውድቀት ዋዜማ መሆኑ የታመነ ነው፡፡

 



ሁለተኛው ምልክት ቤተ መቅደሱን የንግድ ማዕከል ማድረጋቸው ነበር፡፡ የቤተመቅደሱ አገልጋዮችም የእስራኤልን አምላክ አንደ አባቶቻቸው በፍቅርና በቅንዓት ከማገልገል ይልቅ በጥቅም ታውረው፤ ቤተ መቅደሱንም በሀብት መክበሪያ አድርገውት ነበር፡፡ ይህ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን እያታየ ያለ ምልክት ነው፡፡ አገልጋዮች ምንደኞችና ላልተገባ ጥቅም ተላልፈን የተሰጠን ሆነናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በገቢ ራሷን መቻሏን የሚጠላ ማንም ባይኖርም በፋይናንስ ከመጠንከር በላይ ግን በእምነት፣ በጸሎት፣ በመንፈስ፣ በእውነት፣ በሕይወት፣ በተጋድሎ ወዘተ … መጠንከር ይጠበቅበታል፡፡ ዓለምን፣ የጨለማ አበጋዞችንና መልዕክተኞቻቸውን ድል እየነሳች እዚህ የደረሰች በእርሱ ነውና፡፡ ባሏት ይዞታዎች ላይም መገንባት ያለባት ለሰው አካላዊ፣ አእምሯዊና መንፈሳዊ እድገት የሚጠቅም ተቋም እንጂ ሀብት ለማከማቸት ብቻ መሆን የለበትም፡፡ የቤተ መቅደሱ ባለቤት አይሁድን “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፣ እናንተ የሌቦችና የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት” ቢላቸውም በምህረት የተገለጠ ተግሳፁን ናቁ፡፡ እኛም የአይሁድ ወራሾች ሆነን መቅደሱን አቃለናል ተግሣፁንም ንቀናል፡፡

ሶስተኛው ምልክት የመኳንንትን ሥልጣን በመፍራት እውነትን አለመግለጥ ነበር፡፡ ሄሮድስ የወንድሙን ሚስት እስከ ማግባት ኃጢአት ሲሠራ ባህታዊው ዮሐንስ እንጂ ቤተ ክህነቱ ትንፍሽ አላለም፡፡ በዘመኑ የነበረው የአይሁድ ቤተ ክህነት ዘማውያን ባለሥልጣናትን የሚታገሥ ለድሆች የሚራራ ድውያንን የሚፈውስ ንጹሑን ጌታ ግን የሚከስ ነበር፡፡ ለምድራዊ ገዥዎች እጅ የሰጠች ቤተ ክህነት ተቀንዮቷ ለምድራዊ ጌታ ስለሆነ ሰማያዊውን አደራ ለመፈጸም አቅም አይኖራትም፡ ቤተ ክርስቲያን በዓለም ተገልጣ ታየች እንጂ ከዓለም አይደለችም፡፡ እግዚአብሔርን ከሚፈሩ እንጂ ነገ ወደ አፈርነት ከሚቀየሩ ዕቡይ ምድራዊ ገዦች ጋር ኅብረትም የላትም፡፡ እየሆነ ያለው ግን በተቃራኒው ነው፡፡

አራተኛው ምልክት የእግዚአብሔር ባላደራዎች የነበሩት ካህናትና የሕግ መምህራን ሕዝቡን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ በእውነትና በቁርጠኝነት ከመሥራት ይልቅ የልብሳቸውን ዘርፍ በማስረዘምና አሸንክታብ በማብዛት መንፈሳዊ ለመምሰል መሞከራቸው ነው፡፡ የነበሩበትን ግብዝነት ጌታችን ገልፆ ነግሯቸው ነበር፤ ግን አልተመለሱም (ማቴ 23 ተመልከት)፡፡ ካህናተ ሀዲስን ከፈሪሳዊያን እርሾ ተጠበቁ አለን፡፡ ነገር ግን በተቃራኒው በተከለከልነው እርሾ ቦክተን ማዕዳችንን የኮመጠጠ ሞላነው፡፡

አምስተኛው ምልክት በቤተ ክህነቱና በመናንያኑ መካከል የነበረው መቃቃር ነው፡፡ ኤሴያውያን በሚል መጠሪያ የሚታወቁት መናንያን በቤተ መቅደስ የሚፈፀመውን ነውር ከመጠየፋቸው የተነሳ ግንኙነታቸውን ጨርሰው አቋርጠው በዮርዳኖስ በረሃ ተከተው ይኖሩ ነበር፡፡ ጌታችን በበረሃ የጾመው በቤተ መቅደስም ያስተማረው ሁለቱንም አገልግሎት ባርኮ ሊሰጥ ነው፡፡ በዘመናት ቤተ ክርስቲያን የተጠበቀችውም በመናንያን ጸሎትና በመምህራን ትጋት ነው፡፡ ዛሬ ግን ገዳማውያኑ ቤተ ክህነቱን እንደ ዓለማዊ ቆጥረው ቤተ ክህነቱም መናንያኑን ማማከርን ችላ ብሎት የተናጠል ጉዞውን ተያይዘነዋል፡፡ ሁለቱን አስተሳሰሯቸው ያለ መዋቅር እንጂ መንፈስ እንዳልሆነ በግልፅ እየታየ ነው፡፡

ስድስተኛው ምልክት ሢመት ነው፡፡ በሕገ ኦሪት መሰረት የሚሾም አንድ ሊቀ ካህናት ነው፡፡ ቤተ አይሁድ ግን ቤተ መቅደሱ ላይ ሥርዓት ጥሰው ሕግ አፍርሰው አንዱ ሊቀ ካህናት ሳይሞት ሌላ ሾመው ሀናና ቀያፋ በተባሉ በሁለት ሊቃነ ካህናት ይመሩ ነበር፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም አንዲት ቤተ ክርስቲያን ሊኖራት የሚገባ ፓትርያርክ አንድ ብቻ ነው፡፡ አሁንም ግን የሆነውና እየሆነ ያለው ግን በተቃራኒው ነው፡፡

በዚህ ጊዜ ነው አውድማን ሊያጠራ መንሽ የያዘው የተገለጠው፡፡

ዮሐንስ መጥምቅ በአውድማው ላይ ሥልጣን ያለውን መምጣት የገለፀው እንዲህ ሲል ነው፡፡ “እናንተ የእፉኝት ልጆች ከሚመጣው ቁጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ? እንግዲህ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤ በልባችሁም አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ፡፡ እላችኋለሁና ከእነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጆች ሊያስነሳለት ለእግዚአብሔር ይቻለዋል፡፡ አሁንም ምሳር በዛፎች ሥር ተቃጥቷል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል፡፡ . . . መንሹም በእጁ ነው፤ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፤ ስንዴውንም በጎተራው ይከታል፤ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል፡፡”

አንባቢው ያስተውል! በአይሁድ ሕዝብ፣ ገዥዎችና ቤተ ክህነት ዘንድ ይፈፀም የነበረው ጌታ እግዚአብሔርን የሚሳዝን በደል በልዑሉ ቁጣ ለመጠረግ ዋዜማ ነበር፡፡ እኒህ ሁሉ በእኛ መካካል መፈፀማቸውን ያስተዋለ ጥፋት በደጃችን እንደ ቀረበ ይወቅ፡፡ የእግዚአብሔር አውድማ ኢትዮጵያ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን በጊዜ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ ካልተገኘብን በአይሁድ የደረሰ እንደሚደርስብን የማያጠራጥር ነው፡፡ አውድማው ይጠራ ዘንድ ግድ ነው፡፡ እኛ እንዲህ ነን! የነእንትና ዘር ነን! አንፈርስም . . . አንጠፋም በሚል ፉከራ እርስ በርስ በመደላለል የምንኖርበት ሰዓት አብቅቷል፡፡ አሁን ባለ መንሹ ቆሟል፤


ምሳርም በዛፍ ሥር ተቃጥቷል፤ መቆረጥ ያለበት ሁሉ ይቆረጣል፡፡ ልዑሉን በመፍራት የሚኖሩ ግን ከፀጉራቸው አንዲት አትወድቅም፡፡ ለእነርሱ ሞትም ሆነ ሕይወት ለክብር ይሆናል!

ስልክ ይጠራል

ቀሲስ፡- ጤና ይስጥልኝ… እንዴት ከረሙ?

መልስ፡- እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን! በደህና ሰነበቱ ወይ ቀሲስ? ቀሲስ፡- ክብር ይግባው! ደህና ነኝ!

(መሀሉ አይነገርም)

ስንብት

ቀሲስ፡- እንግዲህ ጌታ እግዚአብሔር ምህረቱን እንዲያቀርብ መዓቱን እንዲያርቅ ጸልዩልን? መልስ፡- ዘመነ ዮሐንስን በደኅና ካለፍን ምንም አንሆን አይዟችሁ!

ቀሲስ፡- ዘመነ ሉቃስ ማለትዎ ነው?

መልስ፡- ኧኸ . . . ሉቃስማ አለፈ ዮሐንስን ነው እንጂ!

ቀሲስ፡- ኧረ እባካችሁ እኛ እኮ በጭንቅ አለቅን፡፡ እናንተ ሚስት ልጅ ውላጅ የለ ምንም አያሳስባችሁ፡፡ እኛ ግን እዚህ በጭንቀት አለቅን፡፡

መልስ፡- አዬ እሱን እንኳ ተውት የሚጨነቅ ማን እንደሆነ ባለቤቱ ያውቃል፡፡ ለማንኛውም ዘመነ ላህም አልፎ የሚተካው ዘመነ ንስር ስለሆነ እንደ ንስርነቱ የሚለቀመውን ለቅሞ ሰላም ይሆናል አይዟችሁ!

ቀሲስ፡- እንግዲያው ከሚለቀሙት እንዳንሆን በጸሎታችሁ አስቡን?

መልስ፡- ደግ ዛዲያ ምን ይዘን ኖሯል? አይዟችሁ! ጸሎተ አበው ይጠብቃችሁ! ቀሲስ፡- አሜን!!!

 

“ለእኔም ዘመኑ ቀርቧልና የዚህን መጽሐፍ . . . ቃል በማኅተም አትዝጋው፡፡ ዓመፀኛው ወደ ፊት ያምፅ፤ ርኵሱም ወደ ፊት ይርከስ፤ ጻድቁም ወደ ፊት ጽድቅን ያድርግ፤ ቅዱሱም ወደ ፊት ይቀደስ”

በአዲስ ዓመት መልካም አዲስ ሕይወት!

 

ተጻፈ ኅሊናቸው ላልተቀሰፈ በጳጉሜን 2011 ዓ.ም ቀሲስ ታምራት ውቤ

Read more...

የ “at least” ክርስትና

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን! የ “at least” ክርስትና

 

 

በቅርብ በቅዱስ ጋብቻ አንድ የሆኑ ጥንዶች ስለ ክርስትና ሕይወት ለመወያየት ፈልገው በቢሮዬ ተገናኘን፡፡ ውይይታችን ከተነሱት በርካታ ጉዳዮች የዘመኑን የክርስትና ሕይወት አጉልቶ የሚያሳዩ ሁለት ነጥቦችን እነሆ፡፡

የመጀመሪያው ከእንግዶቹ የተነሳው ሀሳብ በምንኖርበት አገር የሚያስተምሩን ካህን በክርስትና ሕይወት ስንኖር at leastእነዚህ እነዚህ ነገሮችን ልንፈጽም እንደሚገባ ነግረውናል፤ እርስዎስ ምን ይመክሩናል? በሚል ውይይታችንን ጀመርን፡፡ በተቀመጥኩበት የጌታ እግዚአብሔር ፈቃዱ የተገለጠበትን መጽሐፍ ቅዱስን በኅሊናዬ ለመዳሰስ ሞከርኩ፡፡ እናም ላገኘው ያልቻልኩት ነገር ቢኖር at leastበሚል ቀዳሚ ቅጽል የተቀመጠን ትዕዛዝ ነው፡፡ መንግስተ እግዚአብሔርን ለመውረስ የተቀመጠ “minimum requirement” ምን እንደሆነ ማወቅ ብችል ብዬ አሁንም ለማሰብ ሞከርኩ ግን አሁንም መልስ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ ምክንያቱም ያ መስፈርት መንግሰቱን ለመውረስ ካበቃ “minimum requirement” ሊሆን አይችልም፡

፡ ነገር ግን በተለምዶ መምህራነ ወንጌል ክርስቲያኖች ከሆንን at leastይህን ልንፈጽም ይገባናል እያልን ስለምናስተምር፤ አበ ነፍሳትም ልጆቻችንን ስንመክር ልጆቼ “ቢያንስ” ይህንና ይህን ለማድረግ ሞክሩ ስለምንል ምዕመኑን የ “at least” ክርስትና ውስጥ አመቻቸነው፡፡ ምዕመኑም ለሚበልጠው ጸጋ ከሚተጋ ይልቅ “at least” ይህን ይህን እየፈጸምኩ ነው በማለት ለራሱ የጽድቅ መስፈርት አስቀምጦ ተዘናጋ፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ግን “አድርግ አታድርግ፤ ሁን አትሁን” እንጂ፤ at least” ይህን አድርግ ይህን አታድርግ፤ “at least” ይህን ሁን ይህን አትሁን የሚል የለም፡፡ ወጥመድ የማይመስሉ የክፉውን ማዘናጊያና የምኞታችንን ማባበያ ትተን “ንቁ፣ በሃይማኖት ቁሙ፣ ጠንክሩ” የሚሉትን የአባቶቻችን የሐዋርያትን ምክር መስማት ካልቻልን ሊውጠን ፈልጎ ዙሪያችንን ለሚያገሳው አንበሳ ጥሩ ታዳኝ እንሆናለን፡፡ ከእንግዶቹ ጋር የነበረን ውይይት በሌላ ልሳን ስለ ነበር በመጨረሻ የሰጠኋቸው ማሳሰቢያ “anyways do not tell the priest about the at least!” የሚል ነው፡፡

*** do you mind to list yours “at least”?

ሁለተኛው ነጥብ በየጊዜው የእግዚአብሔርን ቃል ለማሰማት በቆምኩባቸው ጉባኤዎች ሁሉ እየታዘብኩ የመጣሁት ምዕመናኑ በእያንዳንዱ ጉዳይ ላይ “ማስረጃ” እንዲቀርብ ያለው ፍላጎትና መምህራንም ምዕመኑን በማስረጃ እያረካን በእምነት ግን እያደኸየን መምጣታችንን ነው፡፡ ይህ በሊቃውንት (በኢትዮጵያ ሊቃውንት ዘንድ ብቻ ማለቴ አይደለም) ዘንድ ቶማሳዊነት ይባላል፡፡ “ጌታ ተነስቷል” ሲባል ጣቴን በችንካሩ ካላገባሁ፤ በእጆቼም የተወጋ ጎኑን ካልዳሰስኩ አላምንም ማለት ነው፡፡ ለሁሉ ማስረጃ ፍለጋ፡፡ ጌታችን ለዚህ መልስ ሲሰጥ “ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን ናቸው” ነው ያለው፡፡ እምነትና ማስረጃ ፍጹም የተለያዩ መንገዶች ናቸው፡፡ እምነት የማስረጃ ጥገኛ አይደለም፡፡ በራሱ ጸንቶ የቆመና፤ ጸንቶ ለማቆምም መሠረት መሆን የሚችል ነው፡

፡ በክርስትና ለሁሉ ነገር ማስረጃ ከፈለግን ከማመን ይልቅ ለመካድ ቅርብ እንሆናለን፡፡ መምህራንም ያሳመንን እየመሰለን በማስረጃ ጋጋታ ከእምነት ምዕመኑን እያራቆትነው ነው፡፡ ማስረጃ አንድን ነገር እውነት ወይም ሀሰት መሆኑን ያሳውቀናል፡፡ ማስረጃ ከእውቀት ጋር እንጂ ከእምነት ጋር ባህርያዊ መስመር አያገናኛቸውም፡፡ በክርስትና በእምነት እንጂ በማስረጃ ምንም ያህል ርቀት እንደማንሄድ ብዙ ማስረጃ ማምጣት ይቻላል፡፡ ግን ከዘረዘርኩ አሁንም ማስረጃ ላቀርብ ነውና በሀሳቤ ተቃርኖ ላይ ልቆም ነው፡፡ ስለዚህ እመን!!!

ይህ በሽታ ሲጀምር አንድ ቃለ እግዚአብሔር በተጠቀሰ ቁጥር ምን ላይ ተጽፏል በማለት ይጀምራል፡፡ ይህ ማለት በሚያስተምረን መምህር ላይ እምነት የለንም ማለት ነው፡፡ ግን እኮ መምህሩ ለጠቀሰው ጥቅስ እንጂ ለሰጠው ማብራሪያና ትንታኔ፤ ላመጣው ትርጓሜና ላመሠጠረው ምሥጢር ማስረጃ አላቀረበም፡፡ ወይስ ጥቅሱን ማሳየቱ ብቻውን ያቀረበውን ትንታኔና የተረጎመውን ትርጓሜ ትክክል ያደርገዋል? ያለው አማራጭ አንድ ነው፡፡ መምህሩን ካመንከው አዳምጠው ካላመንከው አታዳምጠው፡፡

በሽታው እያደገ ሲሄድ ምሥጢራትንና በምሥጢራት የምናገኘውን ጸጋ መጠራጠር እንጀምራለን፡፡ ይህ መጽሐፍ እንደሚል የደረቁ ወንዞች ማለት “እምነት አልቦ ክርስቲያኖች” የምንሆንበት ደረጃ ነው፡፡ የሚታይብንም በልማድ የምንፈጽመው ሥርዓት እንጂ በመንፈስ በእውነትና በመንፈስ የሆነ አምልኮ አይደለም፡፡ የሥርዓት ክርስቲያኖች(canonical Christians) እንጂ መንፈሳዊ ክርስቲያኖች (spiritual Christians) ለመሆን እንቸገራለን፡፡ ፍጻሜውም የጸጋው ባለቤት የሆነውን መድኃኒታችን


ኢየሱስ ክርሰቶስን መጠራጠርን ያመጣል፡፡ ይህም ክህደት ነው፡፡ ዛሬ በቤተክርስቲያን ለምናየው የክርስትና ሕይወት ድርቅ አንዱ ምክንያት ይሄ ነው፡፡ አገልጋዩና ምዕመኑ አይተማመኑም፡፡ ስለዚህ የምንማረውም ሆነ የምናስተምረው ወደ ክህደት ለመድረስ ነው፡፡ ሳናውቀው!!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር!

 

ቀሲስ ታምራት ውቤ ሐምሌ 17 2011

Read more...

ታሪከ አበው፡ ሳሙኤል

Download
Name
Play
Size
Duration
download
ሳሙኤል ክፍል 2
yeneta.info

96.3 MB
1:26:36 min
download
ሳሙኤል ክፍል 1
yeneta.info

83.1 MB
1:16:25 min
download
ሳሙኤል ክፍል 3
yeneta.info

62.7 MB
1:09:26 min

Read more...

እስረኞቹ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!

በተኛበት የዋሻ እስር ቤት ቅዝቃዜ ሰውነቱ ደንዝዟል ለእርሱ ብቻ በሚሰማው ቃል ግን መንፈሱ ግሏል፡፡ አካሉ በደረሰበት እንግልት ደቋል ልቡ ግን እንደ ዓለት ፀንቷል፡፡ የመንፈስ ልጆቹ ዓይን ውስጥ ያየው አንተ ከሌለህ ምን እንሆናለን? የሚለው ጭንቀት የማያንቀላፋ እረኛ የራሳቸውን ፀጉር እንኳ ቆጥሮ የሚያውቅ ጠባቂ እንዳላቸው ካለመረዳት የመጣ እንደሆነ በመረዳቱ የፀናውን እውነት እንደሚገባው አልገለጥኩላቸው ይሆን? ሲል ላፍታ አሰበ፡፡ ከተቀመጠበት በውኃ የላቆጠ የእስር ቤት ወለል ላይ ተነስቶ የእስር ቤቱን ዘብ ለልጆቹ መልዕክት የሚጽፍበት ብዕርና ክርታስ እንዲሰጠው በትኁት ድምጽ ለመነው፡፡ በጭካኔ የደደረው የሮማ ወታደር ልብ በማያውቀው ምክንያት በእስረኛው ላይ መጨከን ተሳነው፡፡ ትንሽ እልፍ ብሎ ከተቀመጠው ጠረጴዛ ላይ ብዕርና ክርታሱን እንዲሁም ቁራሽ ዳቦ አቀበለው፡፡ ኅብስቱን እንደ ተቀበለ እጆቹ እየተንቀጠቀጡ እንባ ባቀረሩ ዓይኖቹ ዘቡን ተመለከተው፡፡ ዘቡ ምን የሚያስከፋ ነገር እንዳደረገ በመደናገር ትኩር ብሎ እስረኛውን ሲያጠናው በዕድሜና በእንግልት ከደከመ ልሳን የሚያስደንቅ ጥንካሬ ያለው ቃል መፍለቅ ጀመረ፡፡ 

 

እኛ አስራ ሁለታችን፣ እናቱና ከገሊላ ጀምሮ የተከተሉት ሴቶች አብረን አጠገቡ ጉብታው ላይ ተቀምጠናል ሕዝቡ ግን ታቹን ሜዳውን ሞልቶታል፤ በግምት የአምስት ገበያ ሕዝብ ይሆናል፡፡ ከፊልጶስና ከእንድርያስ ጋር ጥቂት ቃላት ከተነጋገሩ በኋላ “ይበቃል” ሲላቸውና እርስ በርስ ግራ በመጋባት ሲተያዩ ተመለከትኳቸው፡፡ ወዲያው ጌታችን ፊልጶስ አጠገቡ በዕንቅብ ያስቀመጠውን አምስት ኅብስትና ሁለት ዓሣ ይዞ አሻቅቦ ወደ ሰማይ ዐየና ባረከ፤ ቆርሶም ለሁላችን ሰጠን፤ እኛም ለሌላው እንዲሁ፡፡ የሆነው ሁሉ ልንገነዘበው ከምንችለው በላይ ስለ ሆነብን የጎረስነውን እንኳ መዋጥ አቅቶን ሁላችን ዓይን ዓይኑን በማየት ደንዝዘን ቆምን፡፡ ሕዝቡ በታላቅ ደስታና መደነቅ ተይዞ ከበረከቱ ይሳተፋል፡፡ በዚያ ጫጫታ መካከል “ከሰማይ የወረደ እውነተኛ የሕይወት ኅብስት እኔ ነኝ፤ የሰውን ልጅ ሥጋውን ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፡፡ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ ግን የዘላለም ሕይወት አለው፤ ከሞት ወደ ሕይወት ተሸጋገረ እንጂ ሞትን አያይም” ብሎ በመንፈሱ ቃተተ፡፡ የሚነግረን ቃል ሕይወትና መንፈስ ስለነበር እንዳልገባን ተረድቶናል፡፡ ቃሉን ለመረዳት በራሱ ከላይ ኃይል ያስፈልጋል፡፡ ለካስ ለዚያ ኖሯል በሌላ ጊዜ “ብዙ የምነግራችሁ ነገር ነበረኝ ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ግን ሁሉን ያስታውቃችኋል” ያለን፡፡

 

ተላልፎ በተሰጠባት በዚያች ሌሊትም በመካከላችን ቆሞ ኅብስቱን አነስቶ ባረከ “እንካችሁ ይህ ሥጋዬ ነው ሁላችሁ ከእርሱ ብሉ፣ ደግሞም ወይኑን አንስቶ አመሰገነ ሁላችሁ ከዚህ ጠጡ ይህ ስለ እናንተ የሚፈስ ደሜ ነው ሁላችሁ ከእርሱ ጠጡ፤ ይህን በምታደርጉ ጊዜም ሞቴንና ትንሣኤዬን ታስባላችሁ” አለን፡፡ አሁንም አንተ ኅብስቱን ስትሠጠኝ ከእርሱ ጋር የነበረኝ ጊዜ ትዝ ስላለኝ ነው እንጂ ያንተ በጎነት እንከን ኖሮበት ስላይደለ ቅር አትሰኝ አለው እስረኛው፡፡ የእስረኞቹ ዘብ በሰማው ተደንቆ “እንዲህ በእያንዳንዷ የሀሳብ ልውውጥና ድርጊት ልታስቡት፣ በፍቅሩ ልትቃጠሉና በናፍቆቱ ልትንገበገቡ የቻላችሁ ምን ዓይነት ጌታ ቢሆን ነው? በእያንዳንዱ የኑሮ ሂደት እርሱን እያሰባችሁ በሲቃ መሞላትስ ሕመምና ድካም አይሆንባችሁም? ሕይወታችሁንስ በትካዜ የተሞላ አያደርገውም?” ሲል በመደነቅ እስረኛውን ጠየቀው፡፡ ይህን ሁሉ ለማብራራት ጊዜ ያጥርብኛል፡፡ ይህን ለመረዳት ከእርሱ ጋር ሰው ዓየር ስቦ የሚያስወጣበትን ያህል ቅፅበት ቢኖርህ እመኝ ነበር፡፡ ምሥጢሩ ግን እርሱን በማወቅ፤ ሕይወትና ደስታ የሚለውንም ሐሳብ በምትተረጉምበት መንገድ ይፈታል፡፡ ስሜት ከቃላት በላይ ነው፡፡ ስሜትን መኖር እንጂ ለሌሎች ማጋራት እጅግ ከባድ ነው፤ በውስጡ ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ ለማንኛውም አንተ ይቺን የመጨረሻ ኑዛዜዬን ለልጆቼ ልታደርስልኝ ፈቃድህ ከሆነና እኛ የምንኖረውን ለመኖር ድፍረቱ ካለህ እኛ የቀመስነውን መቅመስ ትችላለህ፡፡ ስለ እኛ ግን በአጭሩ ለማስረዳት በክርስቶስ ወንድማችን የሆነ ጳውሎስ የጻፈውን ላሰማህ፡፡ እንዲህ ይላል “ ነገር ግን በሁሉ እንደ እግዚአብሔር አገልጋዮች ራሳችንን እናማጥናለን፤ በብዙ መጽናት፣ በመከራ፣ በችግር፣ በጭንቀት፣ በመገረፍ፣ በወኅኒ፣ በሁከት፣ በድካም፣ እንቅልፍ በማጣት፣ በመጦም፣ በንጽህና፣ በእውቀት፣ በትዕግስት፣ በቸርነት፣ በመንፈስ ቅዱስ፣ ግብዝነት በሌለው ፍቅር፣ በእውነት ቃል፣ በእግዚአብሔር ኃይል፣ ለቀኝና ለግራ በሚሆን በጽድቅ የጦር ዕቃ፣ በክብርና በውርደት፣ በክፉ ወሬና በመልካም ወሬ ራሳችንን እናማጥናለን፡፡ አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን፤ ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን፤ የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን፤ የተቀጣን ስንሆን አንገደልም፤ ኀዘንተኞች ስንሆን ዘወት ደስ ይለናል፤ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለ ጠጎች እንደርጋለን፤ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው ” ፡፡ በሌላ ሥፍራም “ በሁሉ እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤ እናመነታለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም፤ እንሰደዳለን እንጂ አንጣልም፤ እንወድቃለን እንጂ አንጠፋም፡፡ የኢየሱስ ሕይወት ደግሞ በሥጋችን ይገለጥ ዘንድ ሁልጊዜ የኢየሱስን መሞት በሥጋችን ተሸክመን እንዞራለን፡፡ የኢየሱስም ሕይወት ደግሞ በሚሞት ሥጋችን ይገለጥ ዘንድ እኛ ሕያዋን የሆንን ከኢየሱስ የተነሳ ዘወትር ለሞት አልፈን እንሰጣለን፡፡ . . . ስለዚህም አንታክትም! ነገር ግን የውጪው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል፡፡ የማይታየውን እንጂ የሚታየውን ባንመለከት ቀላል የሆነ የጊዜው መከራችን የክብርን የዘላለም ብዛት ከሁሉ መጠን ይልቅ ያደርግልናልና የሚታየው የጊዜው ነውና የማይታየው ግን የዘላለም ነው” ይላል፡፡ ወንድሜ ሆይ አሁን ፍቀድልኝና ኑዛዜዬን ልጻፍ ከዚያ ፈቃድህ ከሆነ ብርሃንን ታያለህ ብሎ እስረኛው ወደ ሥፍራው ተመለሰ፡፡ የእስረኞቹ ዘብ ፈዞ እየተመለከተ እስረኛው የተቀበለውን ኅብስት በዕድሜ ለጋና ቁጡ የሆነ ሁሉን ለሚያመናጭቅ በነፍስ መግደል ለታሠረ ሌላ እስረኛ ሠጠው፡፡ በለዘበ አንደበትም ገና ብዙ ሥራ ይጠብቅሀል፤ አትሞትም፡፡ ከዚህ ስትወጣ ግን የእግዚአብሔርን ቸርነትና እኔም የነገርኩህን አትርሳ፡፡ 


 

በጭቃ የላቆጠ እጁን ልብሱ ላይና እርስ በእርሱ በማሻሸት ካላቀቀ በኋላ ዓይኖቹን በዋሻው የላይኛው ክፍል ላይ ሰክቶ በመንፈሱ ቃተተ፡፡ “የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ጴጥሮስ እግዚአብሔር አብ አስቀድሞ እንዳወቃቸው በመንፈስም እንደሚቀደሱ፤ ይታዘዙና በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ይረጩ ዘንድ ለተመረጡት መጻተኞች ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ! እውነትን ስላወቃችሁና ሕይወት ስለተገለጠላችሁ እንደሚታዘዙ ልጆች ባለማወቃችሁ አስቀድሞ የኖራችሁበትን ምኞት አትከተሉ፡፡ ይልቁን የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁ በመጠን ኖራችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡ ማንም የሚናገር ቢኖን እንደ እግዚአብሔር ቃል ይናገር፤ የሚያገለግልም ቢሆን እግዚአብሔር በሚሠጠኝ ኃይል ነው ብሎ ያገልግል፡፡ ትጸልዩ ዘንድ በመጠን ኑሩ ፤ ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ፡፡ በእኔ ከእናንተ መለየት በልባችሁ ብዙ ፍርሃት እንደገባ አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን አይዞአችሁ በአንዳች አትሸበሩ፡፡ እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ሁሉ በእርሱ ላይ ጣሉት፡፡ በዓለም ያለን ወንድሞቻችሁ ሁሉ ያን መከራ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት፡፡ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ፡፡ በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ፡፡ እንደ በጎች ትቅበዘበዙ ነበርና አሁን ግን ወደ ነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ ተመልሳችኋል፡፡ ሞት ወደ ወገኖቻችን ለመሰብሰብ የምንጓዘወው መንገድ እንጂ መለያየት አይደለም፡፡ እኔም በአካል ብለያችሁም በመንፈስ ግን ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ፡፡ በማንም አትፍረዱ፤ በመከራ ታገሱ፤ መልካም ለማድረግ አትለግሙ፤ ቃሉ በምልዐት ይኑርባችሁ፤ በእምነት ጽኑ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳመለከተኝ ከዚህ ማደሪያዬ መለየቴ ፈጥኖ እንዲሆን አውቃለሁና፤ ሁልጊዜም በዚህ ማደሪያዬ ሳለሁ በማሳሰቤ ላነቃችሁ የሚገባኝ ይመስለኛል፡፡ ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ፡፡ በፍቅር አሳሳም እርስ በርሳችሁ ሰላምታ ተሰጣጡ፤ በክርስቶስ ላላችሁ ለሁላችሁ ሰላም ለእርሱም ከዘላለም እስከ ዘላለም ክብር ይሁን፡፡ አሜን!” ፡፡ 

ክርታሱን ጠቅልሎ ለእስረኞቹ ጠባቂ ሲያቀብለው ድካም የተለየው፣ ተስፋ መቁረጥ የሸሸው፣ ሞት የሚፈራው፣ ፍርሃት ያልደፈረው ይህ ሽማግሌ ምን ቢያውቅ ነው? ሲል ተገረመ፡፡ ቅድም የነገረውን አስገራሚ ቃላት የጻፈውን ጳውሎስ የሚባለውን ሰው የት ሊያገኘውና ናዝራውያን ስለሚሞቱለት ስለ እርሱ ማወቅ እንዴት እንደሚችል ሊጠይቀው ሲል ከውጪ ስምዖን ጴጥሮስ የሚባለውን እስረኛ አውጡት ሲል ተሰማ፡፡        

 የእስረኞቹ አለቃ ውስጥ ከነበሩት ዘቦች ሁለት አስከትሎ ሽማግሌውን እስረኛ የሚሰቀልበትን አሸክመው ይዘውት ሄዱ፡፡ በመንገድ ላይ ሳለም በግራና በቀኝ ላሉት “ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም የተመለከትነውን እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፡፡ ሕይወት ተገለጠ አይተንማል እንመሰክርማለን፤ ከአብ ዘንድ የነበረውንም ለእኛም የተገለጠውን የዘላለምን ሕይወት እናወራላችኋለን፡፡ እንግዲህ ከጌታ ፊት የመጽናናት ዘመን እንዲመጣላችሁ ኢየሱስ ክርስቶስንም እንዲልክላችሁ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እመኑ፡፡ ኃጢአታችሁም ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ፤ ተመለሱም፡፡ መዳንም በሌላ በማንም የለም፤ እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እመኑ” እያለ በታላቅ ድምጽ ይጮኽ ነበር፡፡ 

የመሰቀያው ቦታ ሲደርስ ዓይኖቹን ወደ ሰማይ አሻቅቦ እያየ “ጌታ ሆይ ይቅርታህን ከጥብርያዶስ ሞገድ ይልቅ ገዝፎ በሰማሁባት ቅጽበት፤ ወጣት ሳለህ በገዛ ፈቃድህ ታጥቀህ ወደ ምትፈልገው ትሄዳለህ በሸመገልህ ጊዜ ግን እጆችህን ትዘረጋለህ የማታውቀው ያስታጥቅሀል ወደ ማትወደውም ይወስድሀል በማለት በምን ዓይነት ሞት እንደማከብርህ የነገርከኝ ቃል እነሆ ደረሰ፡፡ ጌታ ሆይ አንተን ማወቅ የጥበብ ሁሉ ጫፍ ነው፤ አንተን ማመን ክብር ሁሉ የማይተካከለው ማዕረግ ነው፤ ስላንተ መከራን መቀበል ሽልማት ሞትም ሕይወት ነው፡፡ በዚህ ደካማ ሰውነታችን ስላንተ ከዚህም በላይ እንድንሆን የሚፈለግ ቢሆንና ብንሆን እንኳ የፍቅርህን መጠን ሊገልጽልን አይችልም፡፡ ልንሆን የማንችለውን እንድንሆን ስላስቻልከንና ካንተ ጋር እንነግስ ዘንድ ፈቃድህ ስለሆነ እናመሰግንሃለን!!!” 

ጸሎቱን እንደ ጨረሰ መስቀሉ ላይ ሊቸነክሩት ሊያስተኙት ሲሞክሩ የእስረኞቹን ዘብ በዓይኖቹ እየተማጸነ ታገላቸው፡፡ ወታደሮቹ ሲታገሉት የእስረኞቹ ዘብ ላለመሞት ግብግብ እንዳልገጠመ ተረድቶት ወደ ሽማግሌው በመቅረብ በትኅትና ምን እንደሚፈልግ ጠየቀው፡፡ በዕንባ በራሱ ዓይኖቹ የእስረኞቹን ዘብ እየተመለከተ በሚንቀጠቀጥ ድምጽ “አ..አ…አ…አይሆንም እ…እኔ እ…እ…እንደ ጌ…ጌ…ጌ…ጌታዬ ወደ ላ…ላይ ልሰ…ቀል አ..ይ..ገ..ባ..ኝ..ም፤ ኃ..ጢ…አ…ተ..ኛ… ነ…ኝ ….ቁ..ል..ቁ..ል ስ…ቀ…ሉ..ኝ” ሲል ተማጸነ፡፡ የእስረኞቹ ዘብ ብቻ ሳይሆን ወታደሮቹ ጭምር በሽማግሌው ጥያቄ ግራ ተጋብተው ፈዘዋል፡፡ ሽማግሌው ግን ውትወታውን ስላላቆመ የእስረኞቹ አለቃ ፈቃዱን እንዲፈጽሙለት ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ ሽማግሌው ወደ ምንጣፉ ለመተኛት እንደሚቸኩል ሰው ተጣድፎ መስቀሉ ላይ ተኛ፡፡ ሲቸነክሩት ትንሽ ካሰማው የጣዕር ድምጽ ውጪ ምንም የተለየ ነገር አልታየበትም፤ ይልቁን በሀሳብ ርቆ የሚቆዝም ይመስል ነበር፡፡ 

መስቀሉን ካቆሙት በኋላ የእስረኞቹ ዘብ አጠገብ ካለ ቋጥኝ ላይ ዐረፍ ብሎ መጨረሻውን ይጠባበቅ ጀመር፡፡ ሽማግሌው ግን በመስቀሉ ላይ እንኳን ቁልቁል ተሰቅሎ እስከ ሞት ስለተከተለው ጌታው በፍጹም ግለት ይመሰክር ነበር፡፡ ብዙ ቢናገርም ትንፋሹ በደከመበት ሰዓት የተናገራቸው ጥቂት ቃላት ውስጡን ሰርስረው ገቡ፡፡ “አትፍሯቸው! ሥጋን መግደል የሚችሉትን ነፍሳችሁን ግን ምንም ሊያደርጉ የማይችሉትን አትፍሯቸው፤ ይልቁንስ ሥጋንና ነፍስን በአንድ አድርጎ ውደ ገሃነም ሊጥል የሚችለውን እርሱን ፍሩት፡፡ በሚታየውም ሆነ በማይታየው ላይ ሥልጣን ያለውን እርሱን ፍሩት፤ በጊዜም ሆነ ከጊዜ ውጭ የሠለጠነውን እርሱን ፍሩት፤ በሞትና በሲዖል ላይ ሥልጣን ያለውን እርሱን ፍሩት ፡፡ አስቀድማችሁ በቃሉ ለዚህ ዓለም ሳትሞቱ ስለ ቃሉ ትሞቱ ዘንድ አይቻላችሁምና ትጉ” ሲል ሰማው፡፡ የእስረኞቹ ዘብ እርሱ ከተነፈሰ የሽማግሌውን እስትንፋስ የሚነጥቀው ያህል በጭንቅ እየተነፈሰ “እባክህን ስለ ሕይወት ቃል እንደሚገባኝ አውቅ ዘንድ ያ ጳውሎስ የሚባለው ሰው የሚኖርበትን አመልክተኝ” ሲል ተማጸነው፡፡ ሽማግሌውም ፈገግ ብሎ በጭንቅላቱ ወደ አንድ አቅጣጫ አመለከተው፡፡ ወታደሮች አንድን ከትከሻው ጎብደድ ራሱ ገባ ያለ ሰው በሰይፍ ሊቀሉ ከትከሻው ልብሱን እያራቆቱት ተመለከተ፡፡ ያኛው እስረኛ ወደ መገደያው እንደመጣ ሽማግሌውን ትኩር ብሎ ሲመለከተው እንደነበር ያስተታወሰው አሁን ነው፡፡ አንዳች የሚግባቡበት ምሥጢር እንዳለ አስተዋለ፡፡ በመካከል እስረኛው በታላቅ ድምጽ “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይስ ጭንቀት፣ ወይስ ስደት፣ ወይስ ረሃብ፣ ወይስ ራቁትነት፣ ወይስ ፍርሃት ወይስ ሰይፍ ነውን? ብሎ ቃሉን ሳይጨርስ የወታደሩ ሰይፍ አንገቱን ከትከሻው ለየው፡፡ 

የእስረኞቹ ዘብ የሆነውን አይቶ ቁልቁል ወደ ተሰቀለው ሽማግሌ ዘወር ሲል በሚቃትት የደስታ ድምጽ “ስላንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን እንደሚታረዱ በጎች ተቆጠርን፡፡ በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ካሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ሞትም ቢሆን ሕይወትም ቢሆን መላዕክትም ቢሆኑ ግዛትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን ኃይላትም ቢሆኑ ከፍታም ቢሆን ዝቅታም ቢሆን ልዩ ፍጥረትም ቢሆን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቻለው” በማለት ያኛው እስረኛ የጀመረውን ሽማግሌው ሲጨርሰው ሰማው፡፡  ቁልቁል የተሰቀለው ሽማግሌ “ጌታ ኢየሱስ ሆይ ነፍሴን ተቀበላት” ብሎ ሲናገር እና ነፍሱን ሲሰጥ የእስረኞቹ ዘብ በሀዘን እና በቁጭት ሰውነቱ ተወጣጥሮ መዳፉን ሲጨብጥ በቀኝ እጁ መዳፍ ውስጥ የሆነ ነገር እንዳለ ታወቀው፡፡ የሽማግሌው የመጨረሻ ኑዛዜ የተጻፈበት ክርታስ ነበር፡፡

የበጉ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስ በረከት ይደርብን አሜን!

 

                                       ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር              

     

                                           ቀሲስ ታምራት ውቤ                                             2011 ዓ.ም

Read more...

መሻገር

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን !

 

የጳጉሜን ወር ከኖርንበት ለመኖር ተስፋ ወደ ምናደርግበት፤ ከሸኘነው ያለፈ ዓመት ወደ ምንቀበለው አዲስ ዓመት መሻገሪያ ናት፡፡ በባህላችንም በአዲስ ዓመት መባቻ ስንገናኝ የምንለዋወጠው መልካም ቃል ‹‹እንኳንከዘመንዘመንአሸጋገረን››   የሚል ነው ለመሆኑ ከዘመን ወደ ዘመን መሻገር ማለት ምን ማለት ነው? አንድ ሰው ወደ አዲስ ዘመን ተሻገረ የምንለው እንዴት ነው? ወይስ ከዘመን ዘመን መሻገር ማለት ለዘመናት መቁጠሪያነት ጌታ እግዚአብሔር በጠፈር ላይ ያኖራቸውን ዐውደ ፀሐይ፣ ዐውደ ወርኅ እና ዐውደ ከዋክብት ተጠቅመን የቀመርነውን የቀን አቆጣጠር አንድ ዐውድ ጨርሰን ሌላውን መጀመር ነው? 

 

ጌታ እግዚአብሔር ፍጥረታትን በጊዜ እየሠፈረ የፈጠረበት ምክንያት ፊት ያልነበሩ ኋላም ኃላፊ መሆናቸውን ሲያመለክተን ነው፡፡ ፍጥረታትን የሚሰፍር ጊዜ ባይኖር ኖሮ ሁሉ በቅድምና ነበረ ኋላም አያልፍም ለማለት የተመቸ ይሆን ነበር፡፡ ስለሆነም ፍጥረት መለወጥ ማርጀት እንዳለበት ለማጠየቅ ይህን ሂደት የሚሰፍርና የሚያሳውቅ መለኪያ ተሠራለት፡፡ በተጨማሪም ፍጥረታት በጊዜ ውስጥ መገኘታቸው፣ መኖራቸውና ኋላም ማለፋቸው ሠራዒ መጋቢ እንዳላቸው  በማመልከት ፍጥረት ሀለወተ እግዚአብሔርን ጮኾ እንዲመሠክር ያስገድዳል፡፡ ሥሉስ ቅዱስ ግን በባህርያቸው ውላጤ በዘመናቸው ብልየት የለበትምና ጊዜ ይሰፍረው ዘንድ አይችልም፡፡ ነቢዩ ዳዊት “አቤቱ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትህ፤ ሰማያትም የእጅህ ሥራ ናቸው፡፡ እነርሱ ይጠፋሉ፤ አንተ ግን ትኖራለህ፤ ሁላቸው እንደ ልብስ ያረጃሉ እንደ መጎናጸፊያም ትለውጣቸዋለህ፤ ይለወጡማል፡፡ አንተ ግን ያው አንተ ነህ፤ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም” እንዳለ፡፡ መዝ 101(102)፡ 25-27

 

በመሆኑም ከጌታ እግዚአብሔር ለፍጥረት የተቸረ የመጀመሪያ ሥጦታ ጊዜ መሆኑ የጊዜን ክብር የሚያሳይና የሰጪውንም ፍፁም ሥልጣን የሚገልጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ጊዜን እንደ ሰጠ የመንሳት ሥልጣንም የእርሱ ነውና፡፡ ኢሳ 38፡1-5 ፤ዳን 2፡21፤ የሐዋ.ሥራ 1፡7 ጌታ እግዚአብሔር ጊዜ የማይወስነው የፈቀደውን ለማከናወንም የጊዜ መስፈሪያነት የማያስፈልገው ቢሆንም ሥራውን(ልደተ ፍጥረትን) በጊዜ ውስጥ በማከናወን ጊዜ የተሰጠን ለሥራ መሆኑን አሳይቷል፡፡ ጊዜ የማይወስነው በጊዜ ውስጥ ከሠራ ጊዜ የሚወስነንማ እንግዲያው እንደምን ልንጠቀምበት ይገባ? ዘፍ 1፡1

 

ጌታ እግዚአብሔር ጊዜን ምሳሌ በማድረግ የፍጥረትን ህልውና ሂደትና ግብ አሳይቶናል፡፡ በመጀመሪያ ጊዜንና በጊዜ ውስጥ ፍጥረትን በማምጣት ካለ መኖር ወደ መኖር፤ ካለ መታወቅ ወደ መታወቅ ዘመን አሻገረን፡፡ በዚህም ከጊዜ በፊት የነበረው ዘመን የማይቆጠርለት ጥንቱ በዚህ ጊዜ ነው ተብሎ በዘመን የማይሰፈረው ዘመንን የሚሰፍረው ለመኖሪያ ዓለም (space) የማያስፈልገው ራሱን ዓለም አድርጎ የሚኖር እርሱ የነበረበት ነው፡፡ ከዚያ “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ” በማለት የጊዜና የፍጥረት ልደት በአንዲት ቅጽበት ተበሠረ፡፡ ጊዜ ፍጥረትን ፍጥረትም ጊዜን ሳይቀድም ተገኙ፡፡ ኗሪና መኖሪያው፤ ተሰፋሪና መሥፈሪያው፤ ተቆጣሪና መቁጠሪያው በአንዲት ቅጽበት ተገኙ፡፡ ከዚያ አንስቶ ጊዜ ለፍጥረት መሥሪያ ሆኖ እያገለገለ ፍጥረትም በጊዜ ውስጥ እየሰራ ወደ ፍጻሜያቸው ይጓዛሉ፡፡ በመጨረሻም በአንድ ተጠቅልለው ፍጥረትም ጊዜም ያልፋሉ፡፡ ጊዜ ያለ ፍጥረት ፍጥረትም ያለ ጊዜ አልነበረም አይኖርምም፡፡

ያም ሆኖ ግን ከፍጥረታት መካከል በጊዜ ውስጥ እንደሚኖር የሚያውቅ(time concsuessness) ያለው ሰው ብቻ ነው፡፡

 

ከዚህ የመሥሪያ ጊዜ ቀጥሎ የምንሻገር በጊዜ ወደማይሰፈር የዕረፍት ዘመን ነው፡፡ ይህ ዘመን እምነት በጥርጣሬ፣ ዕውቀት በድንቁርና የማይፈተኑበት መበላለጥ፣ መቀዳደም፣ የሌለበት ሁሉ በትምህርት ሳይሆን በባህሪያዊ ዕውቀት ወደ ፈጣሪው የሚቀርብበት ዘመን ነው፡፡ በሌላ አገላለጥ የመጀመሪያው ዘመን እንደታወቅን የማናውቅበት፤ ሁለተኛው ዘመን መታወቃችንን በማመን በመጠራጠርና በመካድ ውስጥ የምንዋልልበት፤ ሦስተኛው ዘመን ደግሞ ንዴተ ህላዌ ፈጽሞ ጠፍቶልን እንደታወቅን የምናውቅበት ዘመን ነው፡፡ ቆሮ 13 ይህ በመለኮታዊው ዕቅድ ፍጥረት የሚያልፍበት የዘመን ሽግግር ነው፡፡ አሁን ባለንበት የመሥሪያ ዘመን ባጋጠመን መታለል ልንሆን የሚገባንን ለመሆን ስላልቻልን ይኸኛውም ዘመን ለሁለት ተከፍለ፡፡ የድንቁርና፣ የድካም፣ የጉስቁልና፣ የልቅሶ የጩኸት የፍዳ ንዑስ ዘመን እና የዕውቀት፣ የኃይል፣ የተሐድሶ፣ የምስጋና፣ የምህረት ንዑስ ዘመን ሆነ፡፡ ይህንንም ማድረግ የቻለ የዘመናት ባለቤት የሆነ እርሱ በሥጋ ልደት የዘመን አካፋይ ሆኖ በመገለጥ ከአንዱ ዘመን ወደ ሌላው አሻገረን፡፡ የምህረት ዘመን ነው ስንል ግን አዋጅ በአዋጅ መለወጡ ለማጠየቅ እንጂ የሥራ(የተጋድሎ) ዘመን አብቅቷል ማለት አይደለም፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች” ቀን በማለት የአሁኑን የተጋድሎ ዘመን ፤ በሌሊት መስሎ ደግሞ የሚቀጥለው(ከሞት በኋላ) ሃይማኖት አጽንቼ የትሩፋት ሥራ ሠርቼ ዋጋ አገኛለሁ የማይባልባትን ዘመን አመልክቶናል፡፡ ዮሐ 9፡4   

 

በዚህ መሠረት ከዓመት ዓመት ስንሸጋገር ልብ ልንለው የሚገባ ዐቢይ ነጥብ ቢኖር ባለፈው ዓመት ምን ሠራሁ? በሚመጣውስ ምን ልሠራ ይገባኛል? የሚለውን ነው፡፡ ባለፈው ካልሠራን፤ ለሚመጣውም የኅሊና ዝግጁነትና ትንሳኤ ከሌለን ዘመን አልተሻገርንም፡፡ መሻገር ውስጥ ምን ጊዜም ለውጥ አለ፡፡ የሚታይ፣ የሚወራለት፣ የሚመሰከርለት፣ በቀጣይ ዘመን ውስጥ ሀልዎት እንዲኖረን የሚያስችል(የሚያበቃ) ሂደት አለ፡፡ በአጭሩ አንድ ሰው በተሰጠው ጊዜ ውስጥ ሥራ ካልሠራ አልኖረም( ህልውና አልነበረውም) ማለት ነው፡፡ በጊዜ ውስጥ ለመሥራት ወይም ላለመሥራት ሥልጣን ተሠጥቶት የተፈጠረ ሰው ብቻ ነው፡፡ ተጠየቅ ያለበትም ለዚህ ነው፡፡ ሌላው ፍጥረት ሁሉ የተገኘበትን ምክንያት በሥርዓተ ተፈጥሮ ፈጽሞ ያልፋል፡፡ ይህን የሚያደርጉ በፈቃድ ሳይሆን በቅድመ ውሳኔ ስለሆነ ምስጋናም ሆነ ወቀሳ የለባቸውም፡፡ ሰው ግን ይለያል፡፡ ምክንያተ ሀልዎቱን ዘንግቶ ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅና፣ ዐውደ ዓመትን በመቁጠር ብቻ ተወስኖ ከኖረ በቁሙ ሳለ ቁጥሩ ከሙታን ነው፡፡ ሙታናቸውን  እንዲቀብሩ ሙታንን ተውአቸው እንዳለ መጽሐፉ፡፡

 

በመሆኑም አንድ ሰው ከዓመት ዓመት፣ ከወር ወር፣  ከሳምንት ሳምንት፣ ከቀን ወደ ቀን ተሸጋገረ የምንለው ምክንያተ ተፈጥሮውን አክብሮ ወደ ቀጣዩ የፍጥረት ዐቢይ ዘመን የሚያሻግረውን የተወደደ ሥራ ሲሠራ፤ በሕይወቱ ላይ ለውጥ ታይቶ ለሌሎችም የለውጥ ምክንያት ሲሆን ነው፡፡ ምክንያተ ፍጥረቱን ዘንግቶ ከፈጣሪው ተለይቶ ከፍጥረተ ዓለም ተጣልቶ የምድርን ጸጋ እንደ ተምች በልቶ ለኖረባትና የሰው ዘር ለሚቀጥልባት የአዳም ማኅጸን ምንም ሳያበረክት፤ እየኖረ እንደሆነ የሚያስብ ከሆነ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ንግግር ከሰውነት ደረጃ ወርዶ የምግብ ማመላለሻ ቱቦ ሆኗል ማለት ነው፡፡

 


እንግዲያውስ ሰውነቱን ያመነ ራሱን በሚሸኘው ዓመት ምን ሠርቶ እንዳሳለፈ በአዲሱ ዓመት ደግሞ ምን ሊሠራ እንዳሰበ መጠየቅ ይኖርበታል፡፡ ሰው ሆይ! ያለፈው ዓመት በስንፍና ማለት መማር ያለብህን ሳትማር፣ መሥራት ያለብህን ሳትሠራ፣ መወሰን ባለብህ ጉዳይ ሳትወስን፣ መለየት ከሚገባህ ሳትለይ፣ ኅብረት ማድረግ ካለብህ ጋር ሳታብር፤ መጀመር ያለብህን ሳትጀምርና ማቆም ያለብህን ሳታቆም ካለፈህ፤ ዘንድሮም ይኸው የሚደገም ከሆነ ዘመን የተሻገርከው እንዴት ነው? የአምና ትኩረትህ ምን ነበር? ፍቅር ወይስ ጥላቻ፣ ይቅርታ ወይስ ቂም፣ ምህረት ወይስ በሌሎች መፍረድ፣ ትጋት ወይስ ሀኬት፣ ቅንነት ወይስ ጥመት፣ ትህትና ወይስ እልከኝነት፣ ንፅህና ወይስ ርኵሰት፣ ንቃት ወይስ ድንዛዜ፣ ትጋት ወይስ ትካዜ፣ እኛ ማለት ወይስ እኔነት…. የቱ ነበር? አሁንስ ወደ አዲስ ዓመት የምትሻገር ይኸንኑ ይዘህ ነው?

 

ዛሬም መሆን የሚገባኝን የምሆነው፤ ማድረግ የሚገባኝንም የማደርገው፤ ከስንፍና ምንጣፍ የምነሳው፤ ካለመወሰን አዚም የምወጣው፤ ከማስመሰል ሕይወት የምላቀቀው መቼ ነው? እያልክ ከራስህ ጋር ትጣላለህ? ራስህን ትጠየፋለህ፣ ትንቃለህ? በራስህ ትማረራለህ? ውስጥህ የተፈጠረውን ሽንፈት የተቀረፀብህን ትንሽነት ለመደበቅ ዙሪያህ ያሉትን ሰላም ትነሳለህ?

 

እስኪ ራስህን ጠይቅ አጠገብህ ላሉት የሰላም፣ የዕረፍት፣ የብርታት፣ የደስታ፣ የስኬት፣ የመልካምነት፣ ምንጭ ነህ ወይስ በተቃራኒው? ከሆድህ የሚፈልቀው የሕይወት ውሃ ነው ወይስ የሞት መርዝ? ወንድሜ ሆይ! ሚስትህ ወደ ግድግዳ ዞራ መኝታዋን በዕንባዋ እንዳራሰች ለማልቀስ እንኳ ተሳቅቃ እንደ ተጨነቀች፤ እህቴም ባልሽ ከባልንጀሮቹ ተለይቶ በትካዜ የወንድ ምጥ እንዳማጠ ስሜቱ ከነገርሽ የተነሳ እንደቆመጠጠ ነው ዘመን የምንሻገረው? ልጆችህ በትናንሽ ዓይኖቻቸው አውሬ እንዳየ ተጨንቀው መሔጃ አጥተው ሲቸገሩ ትንሽ የማይራራ አንጀት ይዘህ መኖር እውነት ዘመን መሻገር ነው? በምቀኝነት ተመርዘህ፣ ቂም አርግዘህ፣ በጥላቻ ተገንዘህ፣ በአዲስ ጨርቅ ላይ አሮጌ ቅዳጅ ለመጣፍ እየዛበርህ ምኑን ዘመን ተሻገርህ? መሆን ለምትችለው ለመትጋት ሀሞት ስታጣ ፈልገህ መርጠህ ባልሆንከው ተቧድነህ ልዩነትን እየሰበክህ፤ ከረገፈ የአባቶችህ አፅም በለስ ከመሰብሰብ ይልቅ ኩርንችት ለመልቀም እያደምህ ምኑን ዘመን ተሻገርህ? ሌት አብራህ የተኛችውን ቀን ዘማ ብለህ እየወገርህ፤ አምኖህ ለክብርህ ከፊት የቆመውን በሥውር ጦማር እያስገደልህ፤ ለጽድቅህ ሚቃትተውን ደሙን መሠዊያው መሃል እያፈሰስህ ምኑን ዘመን ተሻገርህ?

 

ዘመን መሻገር ማለት አዲስ ማንነት መያዝ ነው፡፡ አርዌ ምድር ቆዳው ሲያረጅ ራሱን መሬት ውስጥ ይቀብርና አሮጌውን አውልቆ ጥሎ አዲስ ቆዳ ለብሶ ይወለዳል፡፡ የጌታን ቃሉን የምንሰማ የመንፈስ ቅዱስ ምክር በልባችን አድሮ አሮጌ ማንነታችንን አውልቀን አዲሱን ሰው ለመልበስ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ለእውነትም በሚሆኑ ጽድቅና ቅድስና እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረውን አዲሱን ሰው ልበሱ” እንዳለ፡፡ ኤፌ 4፡24 ዘመን መሻገር ማለት ከክፋት ወደ በጎነት፣ ከሀኬት ወደ ትጋት፣ ከድንቁርና ወደ ማይሻረው እውቀት መወለድ ነው፡፡ እስራኤል ከባርነት ወደ ነጻነት ዘመን እንዲሻገሩ በልዑሉ ክንድ በሙሴ መሪነት ከግብጽ በእግረ ሥጋ ቢወጡም ለአዲሱ ዘመን የተዘጋጀ ልቡና ስላልነበራቸው ዘመን ባለፈበት የኮመጠጠ የግብጽ እርሾ ቦክተው በበረሀ ሻግተው ቀርተዋል፡፡ የዘመናት ባለቤት የሆነውን ይዞ ዘመንን ዋጅቶ መኖር ከሁሉ ይጠበቃል፤ ለትዕግስት ዘመን እንዳለ ሁሉ ለመተፋትም ዘመን አለና፡፡ ምክንያተ ፍጥረትን ሳያውቁ የሕይወት ብርሃን ከሆነው ከእርሱ ተለይቶ መኖር ኑሮ አይባልም፡፡ አባቶች ጌታ ከተወለደባት ጊዜ ጀምሮ አንድ ብለው የቆጠሩ ከእርሱ ጋር ያልነበርንበትን ዘመን እንዳልኖርንበት መቁጠራቸውን ያሳያል፡፡ “አማኑኤል” እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ከሆነ በኋላ የሰው ልጅን ዕድሜ ከፈጣሪው ዕድሜ ጋር አንድ ብለን መቁጠር ጀመርን፡፡ ወደ ዘላለም ከገባው ጋርም ወደ ዘላለም ጊዜን ተሻግረን እንገባለን፡፡

 

ሦስተኛዋ ዘመን በኃጢአት የረከሰ ሰውነት፣ በቂም በጥላቻ የተሞላ ልቡና፣ በእኔ ባይነት የተቀሰፈ ኅሊና የያዘ ተሻግሮ ሊገባባት የሚችል አይደለችም፡፡ ሲያይ የማይታየውን ያልፈራች ሰውንም ያላፈረች ዓይን በሶስተኛው ዘመን ያለውን የሚያስደንቅ ክብር ማየት አይቻላትም፡፡ ሐሜትና ከንቱ ነገርን የጠገበች ዦሮም አዲሱን የበጉን ቅኔ ለመስማት አትታደልም፡፡ ባልንጀራዋን በመሸንገል በመሰሏም በመፍረድ በስድብና በእርግማን የተሞላች አንደበትም የቅዱሱን ስም በህያዋን ምድር ለማመስገን አይፈቀድላትም፡፡ አዲሲቷ ሰማይና አዲሲቷ ምድር ኃጢአት ሊፈፀምባቸው አይደለም ሊታሰብባቸው እንኳ የሚቻልባቸው አይደሉም፡፡ በዚህች ምድር የሚኖሩም ዕረፍት ወደ ሆነችው ሦስተኛዋ ዘመን መሻገር የቻሉ ንፁሐን ብቻ ናቸው፡፡ 

 

የባህረ ሐሳብ ሊቃውንት የጳጉሜን የመጨረሻ ቀን “ምርያ” ብለው ይጠሯታል፡፡ አእዋዲት፣ መድኃኒት ማለት ናት፡፡ አእዋዲት ማለት የምታዘዋውር ማለት ሲሆን፤ መድኃኒት የተሰኘች ጌታ የተወለደባትን ቀን ስለ ምታሳይ ነው፡፡ ዕለተ ምርያ እና የጌታ ልደት የሚውሉ አንድ ዕለት ላይ ነው፡፡ ለምሳሌ ዘንድሮ ዕለተ ምርያ ሰኞ ትውላለች የጌታ ልደት ታህሣስ 29 የሚውለውም ሰኞ ነው ማለት ነው፡፡ ይህም በምሥጢር ዘመን አሻጋሪያችን እርሱ መድኃኒታችን መሆኑን ያመለክታል፡፡ መድኃኒታችን “ኑ ወደ ባህሩ ማዶ እንሻገር” ይለናል፡፡ እንደ ሊቃውንቱ ትርጓሜ ባህር የዓለም ምሳሌ ነው፡፡ የሚያሻግረንን አምነን ከእርሱም ጋር ኅብረት ኖሮን የዓለምን ሥራ ትተን በትንሣኤ ኅሊና ዘመን መሻገር ይኖርብናል፡፡ ሉቃ 8፡22-5 ከዚህም በተጨማሪ የብሉይ ኪዳን መካተቻ እና የአዲስ ኪዳን መባቻ ላይ የነበረውን ንጹሑን፣ ቅዱሱን፣ እውነተኛውን ነቢይና ሐዋርያ፣ ካህንና ሰማዕት፣ ባህታዊና ድንግል ዮሐንስ መጥምቅን ሕይወት አብነት እንድናደርግ በሄሮድስ ታሥሮ የቆየባትን የጳጉሜን ወር እና ምትረተ ርዕሱን እንድናስብ አበው መሥራታቸው ዘመን ከምሥጢር ጋር ያለቸውን ዝምድና እንድናውቅ ለመጠቆም ነው፡፡ ዮሐንስ ሦስተኛውን ዘመን እውን ወደ ሚያደርገው ሙሽራ ሙሽራይቱን ለማድረስ መንገዱን ጠርጓል፡፡ የፈቀዱትን አዘጋጅቷል፣ ደስታውም ተፈጽሞለታል፡፡ የሰሙትም ወደ ምህረት ዘመን ተሻግረው የአባቶቻቸውን ተስፋ ፍጻሜ ዐይተዋል፡፡  አባቶቻችን ከቃል ትምህርት ባለፈ በዕለት ተዕለት ሕይወታችን ውስጥ በሚከሰተው ዓውደ ዓመታችን ታላቅ ምልክትን ትተውልን አልፈዋል፣ እኛ ግን አላስተዋልንም፡፡ ጌታ “ሰማዩ አቀላልቷል ዛሬ ይዘንማል ትላላችሁ፤ የሰማዩን ፊት ታውቃላችሁ የዘመኑን ምልክት መለየት እንዴት አቃታችሁ” እንዲል፡፡ ዘመን ሳንሻገር ስንት ዘመን እንዳሻገርን ማን ይቁጠር? ለማንኛውም . . . 

 

 

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር

 

                                           ቀሲስ ታምራት ውቤ                                             2011 ዓ.ም

Read more...

ታሪከ አበው: ​ሩት

Download
Name
Play
Size
Duration
download
ሩት ክፍል 3
yeneta.info

55.4 MB
40:22 min
download
ሩት ክፍል 2
yeneta

96.9 MB
1:10:33 min
download
ሩት ክፍል 1
yeneta

48.1 MB
34:37 min

Read more...
Subscribe to this RSS feed

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ