Login
Main menu

Items filtered by date: June 2026

ታሪከ አበው: ​ሶምሶን

Download
Name
Play
Size
Duration
download
ሶምሶን
yeneta

49.5 MB
1:03:21 min

Read more...

ታሪከ አበው: ​ጌዴዎን

Download
Name
Play
Size
Duration
download
ጌዴዎን ክፍል ሁለት
yeneta

45.4 MB
56:52 min
download
ጌዴዎን
yeneta

64.3 MB
1:23:19 min

Read more...

ታሪከ አበው: ​ኢያሱ

Download
Name
Play
Size
Duration
download
ኢያሱ ከፍል 3
Yeneta

52.5 MB
1:08:06 min
download
ኢያሱ ከፍል 2
My Recording

101.7 MB
1:14:04 min
download
ኢያሱ ከፍል 4
yeneta

120.2 MB
1:27:30 min
download
ኢያሱ ከፍል 1
yenta

32.6 MB
41:38 min

Read more...

ፍና ቅዱሳን

መጽሐፉን ለማግኝት 

+251 923976850

+251 911249756

ከመጽሐፉ የተወሰደ 

 

‹‹የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፤ የኑሮአቸውን ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው ፡፡ ዕብ. 13÷7

The paradise ወይም The Garden of the Fathers በሚለው ታላቅ መጽሐፍ፤ የእስክንድርያው ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ፤ የሄሊያ ፓሊስ ሊቀ ጳጳስ ጳላድዮስና ቅዱስ ጄሮም፤ ዘመናቸው ታላቅ የቅድስና ሕይወትን በመምራት ይታወቁ የነበሩ አበውን በአካል በማግኘትና፤ በአካል ለማግኘት ያልቻሉትንም ከደቀ መዛሙርቶቻቸው በመጠየቅ የተጋድሎ ሕይወታቸውንና ድንቅ የሆኑ ምክሮቻቸውን መዝግበው ትተውልናል፡፡ 

በአባቶች ዘንድ የቅድስናን ሕይወት ለመኖር የነበረን ቁርጠኝነት፤ ለወጣንያን የሥጋ ፈቃድን መቆጣጠርና የቅድስናን ሕይወት መለማመድን የሚያሳዩበት መንገድ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ለቃኘው ኅሊና እጅግ መሳጭ ነው፡፡ ሰውነቱን ለእግዚአብሔር ሕያውና ቅዱስ መስዋዕት አድርጎ ለማቅረብ ለሚመኝ ሁሉ የቅዱሳንን ሕይወት ከማንበብ የሚበልጥ ነገር አይገኝም፡፡

የንስሐቸው ጥልቀት ልብን ይሰብራል፤ የተጋድሏቸው ትዕግሥት ከዓለት ይልቅ ይጸናል፤ ምክርና ተግሣፃቸው የልብን ሸለፈት ለመግረዝ  ከባልጩት ይልቅ ይሰላል፤ ለጌታ እግዚአብሔርና ለሰው ልጅ ያላቸው ፍቅር ዕንባን በዓይን ይሞላል፤ ትኅትናቸው በትዕቢት ያበጠ ኅሊናን ያፈርሳል፤ ጸሎታቸው እንደ በረሃ የደረቀ ሰውነትን ያረሰርሳል፡፡ እምነታቸው ሕሙማነ ሥጋ ወነፍስን ለመፈወስ፤ የዲያብሎስንም ወጥመድ ለመበጣጠስ በልዑሉ ፊት ብርቱ ነው፡፡ ለእኛ የሕይወት መምህራን የክርስትናም አብነቶች ናቸው ቅዱሳን፡፡ 

ቤተክርስቲያን የቅዱሳንን ታሪክ የምትዘግበው ታሪክ የማስተማር ዓላማ ኖሯት አይደለም፡፡ ያ ቢሆን ኖሮ በቤተክርስቲያን ያልተመዘገቡ የስንቶች ታሪክ ታልፎ አይቀርም ነበር፡፡ ዋና ዓላማዋ ከቅዱሳን ሕይወት እንድንማርና የእነርሱን የተጋድሎ ጥበብ እንድንወርስ ነው፡፡

የዚህ መጽሐፍ ዓላማውም፡-

ሀ. በወንጌል በቃል (theory) ደረጃ ተቀምጦ የምናየውን ክርስትና እንዴት በተግባር መተርጎም (practical) እንደሚቻል ለማመላከት

ለ. የክርስትና ሕግ ከዚህ ዓለም ጠባይና ከሰው ድካም አንጻር ሊፈፀም የማይችል ሕግ ነው ብሎ ለሚያስብ፤ ጌታ እግዚአብሔር ሊፈፀም የማይችል ሕግ እንዳልሰጠንና፤ በሚደንቅ ጽናት የክርስትናን ሕይወት ኖረው ያለፉትን በማየት ከመንፈስ ዝለት ለመራቅ፤

ሐ. መጽሐፍ ቅዱስንም ሆነ ሌሎች ቅዱሳት መጻሕፍትን ለምናነብ ሁሉ እንዲሁ በልማድ፤ ለእውቀት፣ የቋንቋ ክህሎትን ለማዳበር ወዘተ... ሳይሆን በእያንዳንዷ ነጥብ ራሳችንን በመመርመርና ከሕይወታችን ጋር በማገናኘት መሆን እንዳለበት ለማስገንዘብ ታስቦ የቀረበ ነው፡፡

ይህን መጽሐፍም ሆነ ሌሎችን ተመሳሳይ መጻሕፍትን የሚያነብ ሁሉ ዓላማውን መሳት የለበትም፡፡ ባወቅነው መጠን መጠየቅ አለና በተረዳነው ለመኖር መጋደል ይጠበቅብናል፡፡ በወንጌል የተገለጠው ክርስትና በተግባር ተፈጽሞ የምናየው በቅዱሳን ሕይወት ነው፡፡

ክርስትና የሕያው እግዚአብሔርን ልጅ ክርስቶስ ኢየሱስን መምሰል ነው፡፡ የቅዱሳን ምክር ደግሞ እኛ እርሱን እንደመሰልን እኛን ምሰሉ፤ በዕለት ተዕለት ኑሯችሁም እግዚአብሔርን ለመምሰል ራሳችሁን አስለምዱ የሚል ነው፡፡ ይህን ቋሚ የኑሮ መርሕ በማድረግ በየጊዜው የሚታይ ለውጥ ማሳየት ከክርስቲያን የሚጠበቅ ነው፡፡ ብዙዎቻችን መለወጥን አብዝተን እንፈልጋለን፡፡ የዘወትር ጥያቄያችንም እንዴት መለወጥ እችላለሁ? የሚል ነው፡፡ እውነታው ደግሞ የዚያኑ ያህል ለውጥን፤ ጠባዬ የምንለውን አሸንፈን በወንጌል አዲስ ሰው መሆንን አጥብቀን እንፈራለን፡፡ ለውጥ እንዲሁ አይመጣም፡፡ ለመለወጥ ማመን፣ መሻት፣ መወሰን ከዚያም ተጋድሎ ያስፈልጋል፡፡ በቅዱሳኑ ሕይወት የምናየውም ይኸው ነው፡፡ 1ጢሞ. 4÷ 8 ፤ 1ቆሮ 11÷1

የቅዱሳንን ታሪክና የኑሮ ፍሬ ከያዘው <<The Paradise>> ወይም <<The Garden of the Fathers>> መጽሐፍ ላይ የተወሰዱ የተወሰኑ ታሪኮች በዚህ መጽሐፍ ተካተዋል፡፡ ከእያንዳንዱ ታሪክ ለጥቆም ለሁሉም ሊመጥን በሚችል ደረጃ የተወሰኑ ማብራሪያዎች ቀርበውበታል፡፡ በታሪኮቹና በማብራሪያው ውስጥ፡- እውነተኛ ንስሐ ከተለምዶ የከንፈር ኑዛዜ ምን ያህል እንደሚለይ፤ የተሻለውን ስለ መምረጥ፣ ውሳኔ በክርስትና ውስጥ ምን ያህል ሥፍራ እንዳለው፣ በትንሹ ለምናማርርም በመከራ መታገስ ምን እንደሚመስል፣ ምክር መስማትና ተግሳፅን መቀበል ሕይወትን እንዴት እንደሚለውጥ፣ ራስን ለሌሎች አሳልፎ መስጠትና በክርስቶስ የሆነ ፍቅር የማይቻለውን እንዴት እንደሚያስችል፤ የይቅርታን ታላቅ ኃይልና በትዕቢትም የሚገጥመንን ውድቀት ለመዳሰስ ተሞክሯል፡፡ በእያንዳንዱ ታሪክ ላይ የቀረበውን መንፈሳዊ ልምምድም በአቅማችን ግን በጽናትና በታማኝነት ለመለማመድ እንድንጥርም ተጋብዘናል፡፡

የእውነተኛ መንፈሳዊ መጻሕፍት ምንጭ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነውና፤ መጽሐፉን ያዘጋጀሁት ከሚያነቡት ከብዙዎች ራሴን እንደ አንዱ አድርጌ ነው፡፡ የሁላችን መምህር እርሱ ነው፤ ሁላችን ደግሞ ደቀ መዛሙርት!

መጽሐፉን ስናነብ ቢያንስ አንድ ለሕይወታችን የሚጠቅም ነገር እንድናገኝ አምላከ ቅዱሳን ይርዳን!

መልካም ንባብ !

ቀሲስ ታምራት ውቤ

ነሐሴ 2008 ዓ.ም

 

Read more...

ገብር ሔር

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ገብር ሔር፡-  ይህች ዕለት ከልዑል እግዚአብሔር የተለያያ ጸጋን(ሥጦታን) የተቀበልን ሁሉ  አንደየሥራችን ምንሞገስባት አልያም የምንወቀስባት ዕለት ናት፡፡ ሁለቱም ለጥቅማችን እንጂ ለጥፋታችን አይደለም፡፡ 

ምስባክ፡- ከመ እንግር ፈቃደከ መከርኩ አምላኪየ

        ወሕግከኒ በማዕከለ ከርሥየ

        ዜኖኩ ጻድቀከ በማኅበር ዐቢይ፤   መዝ ፴፱፡፰

ትርጉም፡- አምላኬ ሆይ ፈቃድህን እገልጥ(አደርግ) ዘንድ ወደድሁ

         ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው፤

         በታላቅ ጉባኤ ጽድቅህን አወራሁ፡፡

- አምላኬ ሆይ ፈቃድህን ቃል ከግብር አስማምቼ እገልጣት ዘንድ ወደድሁ፡፡ እንዲህ የተዋቡ ቃላትና ሀሳቦች ሊፈልቁ የሚችሉት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር ህብረት ካደረጉ ልቦች(አልባብ)ብቻ ነው፡፡ከሁሉ አስቀድሞ የጌታ እግዚአብሔር ፍቃዱ ምን እንደሆነ አውቃ ትገዛለት ዘንድ ነፍስ በትህትና ወደ ቃሉ ማዕድ መቅረብ ያስፈልጋታል፡፡ ጌታም በመጽሐፍ በሊቃውንት(ካህናት) አፍ ፈቃዱ ምን እንደሆነ አስታውቋል፡፡

        ሰው መንፈሳዊ ሥራን መስራት የሚጀምረው ነፍሱ ከፈቃደ እግዚአብሔር ጋር መስማማት ስትጀምር ነው፡፡ ፈቃደ ነፍሳችን ለፈቃደ እግዚአብሔር ሲገዛ፤ፈቃደ ሥጋችን ደግሞ ለፈቃደ ለነፍስ ይገዛል፡፡

       ሰው በሥጋው ብቻ ሊፆም፣ሊጸልይ፣ሊሰግድ፣ሊያስቀድስ፣የጌታን ሥጋና ደም ሊቀበል በአጠቃላይ አምልኮተ እግዚአብሔርን ሊፈፅም ይችላል፡፡ ኖረንበታልም፡፡ በዚህ ሁሉ ወስጥ ግን በነፍስ መማረክ በመንፈስ መንበርከክ ከሌለ የሚጠቅም አይደለም፡፡

       አንድ ሰው ራሱን ወይም ሌሎችን ከብርቱ ችግር ለማዳን ተጨንቆ፤ ወይም ለራሱም ሆነ ለሌሎች እጅግ የሚጠቅም ነገር አውቆ መልእክት ለማስተላለፍ እጅግ ዘመናዊ የሆነ የእጅ ስልኩን(Cell Phone) ቢያወጣ ያለበት ሥፍራ ግን ኔትወርክ ባይኖረው ምን ሊያደርግ ይችላል? ሙከራው ሁሉ ፋይዳ ቢስ ሲሆን ጭንቀቱን ይበልጥ ቢያባብስበት እንጂ የስልኩን ቀፎ መያዙ መፍትሔ አያመጣለትም፡፡ አንዲህ ዓይነት የአንጎልን ንዝረት የሚጨምር ገጠመኝ ሊኖረን እንደሚችል ጸሐፊው ይገምታል፡፡ የዚያን ቀኑን ስሜት እንድታስታውስም በትህትና ይጠይቃል፡፡ የስልክ ቀፎ የያዘ ሁሉ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ሆነ ማለት አይደለም፡፡ በኛም ቀፎው ሥጋችን ኔትወርኩ ነፍሳችን መንፈሳችን ነው፡፡  ወይም ዓይነ ሥውር ለሆነ ሰው የንባብ መነፅር ቢያደርጉለት እንደማይጠቅመው ነፍስ የእግዚአብሔርን ብርሃን ማየት ከተሳናት ለሥጋ ለብቻው አይቻለውም፡፡

         ጌታችን ለሳምራዊቷ ሴት የገለፀላትም ይህንኑ ነው፡፡ “…እግዚአብሔር መንፈስ ነው፤ የሚሰግዱለትም(የሚያመልኩትም) በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት(ሊያመልኩት) ያስፈልጋቸዋል፡፡ ዮሐ 4፥20-26

        የአዳም ዘር ትምክህት የክርስቶሳውያን ሁሉ እናት በምንም ምን ርኵሰት የሌለባት እመቤታችን ወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም ራሷን ለዓለም ያስተዋወቀችው “ነፍሴ እግዚአብሔርን ታከብረዋለች፤መንፈሴም በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች” በማለት ነው፡፡ ሉቃ1 ፥47


 

       ኔትወርክ ስናገኝ ስልኬ ሠራ እንደምንል፤ነፍስ ለእግዚአብሔር በመገዛት ከመለኮታዊው ፈቃድ ጋር ህብረት ስታደርግ ሥጋም ይከተላታል፡፡ የነፍስም ቅድስናዋ በሥጋ ገዝፎ ይታያል፡፡ የባትሪ ብርሃን በውስጡ ካለው ድንጋይ እንጂ ከአምፖሉ እንደማይገኝ በነፍስ ላይ የሚገለጠው መለኮታዊ ኃይል በሥጋ ተገልጦ በረከት ይሠጣል ተዐምራት ይሠራል፡፡

      በሠለጠነው ዓለም Satelait phone የሚሉት ከሳተላይት ጋር የተገናኘ ተንቀሳቃሽ ስልክ አለ፡፡ እርሱን የያዘ ሰው በየትኛውም ስፍራ ቢሆን ወደፈለገበት መልእክቱን ማድረስ እንደሚችል ይታመናል፡፡ ይህም ከተራው ስልክ የተለየ ያደርገዋል፡፡

     በቅዱሳንም እንዲሁ ነው በዓሣ አንበሪ ሆድ ሆነ በምድር ጉድጓድ፤ በአድማስ ጫፍ ሆነ በበረሃ፤ በቤተመቅደስም ሆነ በዋሻና በፍርኩታ ውስጥ ቢሆኑ ከአምላካቸው ጋር ለመገናኘት የሚያግዳቸው ነገር የለም፡፡ በሁሉ ሥፍራ እርሱ ከእነርሱ ጋር እነርሱም ከእርሱ ጋር ናቸው፡፡ ትን.ዳን 6፥1-23፤ትን.ዮናስ 2፥1-11

     የቅዱስ እግዚአብሔርን ፈቃድ በነፍስ በሥጋ በመግለጥ ይኖር የነበረ የከበረ አባት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ንግስቲቱን በሠራችው ግፍ አውግዞ በተጣላችው ሰዓት አማላጅነት የመጡ አባቶች የንግስቲቱን ቁጣ ሲነግሩት የሠጣቸው መልስ ወትረ ድንቅ የሚያሰኝ ነው፡፡ እኒያ ወርቅ ከናፍር እንዲህ አሉ “ ከቶ ምን አለቻችሁ? በምንስ ዛቻ ላከቻችሁ? ከቶ በእኔ ላይስ ምን ልታደርግ የምትችልበት ሥልጣን አላት? ምግብ በመከልከል በረሃብ እቀጣዋለሁ አለችን? ሰው በእንጀራ ብቻ እንደማይኖር ከጌታዬ ሰምቻለሁ! በሰውነቱ መከራ አመጣለሁ አለችን? በሥጋዬ የጌታን መከራ ተሸክሜ እንድኖር አውቃለሁ! ግዞት፣ስደት ነውን? ዓለም በሞላው የእግዚአብሔር ነው! ሞት ነውን? ወደ ጌታዬ ለመሔድ በናፍቆት የምጠብቀው ሠረገላ ነው፡፡”

     እኒህ ናቸው ከነፍስ ውበት ከመንፈስ ቅድስና የሚፈልቁ ቃላት፤ከጌታ እግዚአብሔር ጋር በፈቃድ በመስማማት የሚቀዱ ምሥጢራት፡፡

- ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው፡፡ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በሲና ኮረብታ በድንጋይ ጽላት የተፃፉ ሕግጋቱን ለነቢዩ ሙሴ ሲሠጠው ዓላማው ትዕዛዛቱን ወደ ሰዎች የልብ ጽላት ለመገልበጥ ነበር፡፡ አልሆነም፡፡ ስለህጉ መልካምነትና ሕዝቡ ግን በመንፈስ ደካሞች ከመሆናቸው የተነሣ እንዴት ይሻር እንደነበር ቅዱስ ጳውሎስ አብራርቷል፡፡ ሮሜ 7፥7-25፤2ቆሮ 3፥1-ፍፃሜ

          በመንፈስ ደካሞች ለሆኑ የእግዚአብሔር ሕግ ሸክም ነው፡፡ ለትጉዎች ግን ሕጉ ሰላምና ተድላቸው ነው፡፡ መዝ 118፥77 እና 165 እውነተኞችም የእግዚአብሔርን ሕግን የሚጽፉት በልባቸው ጽላት ነው፡፡ አስታዋሽ አያስፈልጋቸውም በቀንና በሌሊት ትዝታቸው ነውና፡፡ መዝ 1፥2፤ መዝ 118፥97

          ወገኖቼ ክርስቲያኖች ራስን መመርመር በዚህ አለ፡፡ በኑሮአችን የእግዚአብሔርን ህግጋት የምናያቸው እንዴት ነው?..ከባድና አስቸጋሪ ሊፈፅሙ የማይችሉ፤ አሰልቺና የመኖር ነፃነትን የሚጋፉ፤ሁሉን በማድረግ ውስጥ የሚገኝን ደስታ የሚነጥቁ ፤በጭንቀት፣በሀዘን፣በፀፀት፤ራስን በመውቀስ ባህር ውስጥ የሚደፍቁ፤ እድገትን ሥልጣኔን በኑሮ መሻሻልን የማይፈቅዱ ወዘተ…ወይስ በተቃራኒው ቀላልና በደስታ ሊፈፀሙ የሚችሉ፤ ተወዳጅና የአእምሮ ነፃነት የሚያጎናፅፉ፤ ሁሉን በማድረግ ውስጥ ካለ ፀፀት የሚያተርፉ፤በተስፋ፤በሀሴት በራስ እርግጠኛ በመሆን በመልካም ምርጫ ባህር ላይ የሚያንሳፍፉ፤ ስግብግብነት የሌለው እድገትን፤ክህደት ያልነገሠበት ሥልጣኔን፣ርኵሰት ያልበከለው የኑሮ መሻሻልን የሚደግፉ?...

እኛም ሆነን ልጆቻችን ህገ እግዚአብሔር ከልባችን እየደበዘዘ በሔደ ቁጥር ግብራችን ከእንስሳ፤ ጠባያችን ከአውሬ የከፋና ሌላ አጥፊ ሳይነሣብን እርስ በርሳችን ተባልተን እናልቃለን፡፡


 

       እንኳን በነፍስ በሥጋ ለሚያከብረን ሕገ እግዚአብሔር ቀርቶ ለሕገ መንግሥት፤ለማኀበራዊ ሕግ፣ለትራፊክ ሕግ፤ለመሥሪያ ቤት ሕግ፤ ለማኅበር ሕግ ፣ ለዕድር ሕግ ወዘተ…ስንገዛ አይደለም የምንኖር፡፡ ስንቱን አምነንበት ነው የተቀበልነው? ስንቱስ ጠቃሚያችን ነው? ግን ለግማሹ ጠቃሚ በመሆኑ ለግማሹ በይሉኝታ ስንገዛ እንኖራለን፡፡ ውጤታቸውን ስንመዝን ግን ሁሉ ጊዜያዊ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሕግ ግን ዘላለማዊ ክብር የሚያስገኝ ነው፡፡ የሚገርመው ግን ለሰው ሕግ ስንል የእግዚአብሔርን ሕግ ለመጣስ ቅንጣት የማይከብደን መሆኑ ነው፡፡ ለዕድር ስብሰባ ሲል የሳምንቱን ዕለታት በሰላምና በጤና ስለማለፉ የሚያመሰግንበትን ዕለተ ሰንበትን የሚሽር ክርስቲያንን ክርስቲያን ብዬ እጠራ ዘንድ እንዴት ይቻለኛል? ሕጉ በልባችን ሊቀረፅ ቀርቶ በጆሮአችን በቅጡ ላለማለፉ እልፍ ነጥቦች መጥቀስ ይቻላል፡፡ያለ ዕድር መኖር ትችላለህ ያለ እግዚአብሔር ግን ትጠፋለህ፡፡

በዘመኑ ፍፃሜ ከሰማያት የወረደው ከድንግል ማርያም የተወለደው ኢየሱስ ክርስቶስ የልብ ጸላቶችን ቀርፀን ወደ ተራራው ወደ እርሱ እንወጣ ዘንድ አዘዘን የፍቅርን ህግ ይፅፍብን ዘንድ በሚያስፈራና በሚያስደነግጥ ድምፅ አልተናገረንም፤ ልጆቼ እያለ በልዝብ ቃል ፍቃዱን አስታወቀን እንጂ፡፡ በነፋስና በጢስ በጭጋግና በጨለማ ውስጥ ተሰውሮ አልወረደም፤ ፊትለፊት ተናገረን እንጂ፡፡ በመለኮታዊው እሳት የቀራንዮ ኮረብቶች አንደ ደብረ ሲና አልቀለጡም በእኛ ልብ ላይ የተገሸረ የኃጢአት ድንጋይ ተወገደ እንጂ፡፡

በልባችን ከእግዚአብሔር ሕግ ይልቅ የሚዘከር ከፍቅሩም በላይ ትዝታ ሊሆን የሚችል የከበረ ምን ነገር ይገኛል?

- በታላቅ ጉባዔም ጽድቅህን አወራሁ፤- ፈቃዱን የሚወዱ ሕጉንም በልባቸው የጻፉ ሰዎች ለምስክርነት ይጠራሉ፡፡ እኒህ በእውነት የእግዚአብሔርን የፍቅሩን ጥልቀት የፈቃዱን መልካምነት የሕጉንም በጎነት በሕይወት ያውቃሉና ይመሰክሩ ዘንደ ይገባቸዋል፡፡ እግዚአብሔር ቸር እንደሆነ ቀምሳችሁ እዩት ለማለት ቅድሚያ መቅመስ ያስፈልጋል፡፡ የከንፈር መስካሪዎች በእግዚአብሔር መንግሰት ሥፍራ የላቸውም፡፡ በከንፈሩ የሚያከብር በልቡ የሚክድ በእርሱ ዘንደ የተነቀፈ ነው፡፡ ቃሉ “በልብህ አምነህ በአፍህ ብትመሠክር“ ማለቱን አንዘንጋ፡፡ ማቴ 15፥8 ፤ሮሜ 10፥9-10

        ታላቅ ጉባዔ ለተባለ የሰው ዘር የእግዚአብሔር ልጅ ከኃጢአትና ከሞት ሊያድነው እንደ ተገለጠ እንመሰክር ዘንድ ተመርጠናል፡፡ ጽድቃችን ሰላማችን ሕይወታችን እርሱ ነው፡፡ የሰውን ዘር በሙሉ በእርሱ በኩል ወደሆነ ጽድቅ መጥራት ለጳጳሳት፤ለካህናት፣ለመምህራን፣ለዲያቆናት ብቻ የተተወ ኃላፊነት ሳይሆን ክርስቲያን የሆንን ሁሉ ግዴታ ነው፡፡ በሰው ጉባዔ ፊት አምኖ ለሚመሰክር እርሱ ደግሞ በሰማይ መላእክት ጉባኤ ፊት ይመሰክርለታል፡፡ ማቴ 10፥32

       ምስክርነታችንም በሦስት ወገን ነው፡፡ በቃል በማስተማር፣በህይወት በመኖር፣አስከሞት ድረስ በመታመን፡፡ የመጀመሪያዎቹ ሁለቱ በሰላምም ሆነ በመከራ የክርስትና ዘመን የምንፈፅማቻው ግዴታዎች ናቸው፡፡ ሦስተኛው ግን ስለእርሱ ደምን ለማፍሰስና በሞታችን ለመመስከር የተገባን ሆነን ስንገኝ ነው፡፡

      የከንፈር ምስክሮችና የእውነት(የጽድቅ) ምሥክሮች በሥራቸው የተገለጡ ናቸው፡፡ እውነተኞቹ ሁሉ ሰው በመፈጠርና በመዳን ረገድ የተሰጠው ክብርና ትኩረት እኩል አንደሆነ ሰለሚያምኑ ለሰው ፊት አያደሉም፡፡ ለረብና ለጥቅም የሚሠሩ ምንደኞች፤ የመኳንንትና የወይዛዝርት የድግስ ጌጦች፤ በከንቱ ውዳሴ፤ኔሻን ያሸበረቁ ሞኞች አይደሉም፡፡ ሥልጣን ወጥመድ ዘርና ጎሳን መለየትም ደዌ መሆኑን ያውቃሉ፡፡ ሰውን ለማስደሰትም ሆነ ለማሳዘን ለማክበርም ሆነ ለማዋረድ ሆን ብለው አይናገሩም፡፡ አንደቃሉ ይመክራሉ እንደ ሕጉ ይገስፃሉ ይዘልፋሉ፡፡ የሚጠገን ይጠገናል የሚሰበርም ይሠበራል፡፡ ርኵሰትን የሚፈልግ ወደርኵሰቱ ጽድቅን የሚሻም ወደ ጽድቁ ይሔዳል፡፡

       በሰው ፊትም የሚታሰቡት ሞገደኞች፣ዕብዶች፣ጊዜን ያልዋጁ ቂሎች አንዳንዴም የሰውን ክብር የማያውቁ ዋልጌዎች ተደርገው ነው፡፡ በዚህ ግርዶሽ ስንት የእውነት መልእክተኞች አንደ ዋዛ አመለጡን፡፡ የእነርሱ ቃል ግን “ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዘት ይገባል” ሕይወት ተገለጠ ዓይተንማል፤ ዓይኖቻችን ያዩትን በጆሮአችን የሰማነውን እጆቻችንም የዳሰሱትን እርሱን እናወራላችኋለን” እያለ ለዘላለም ይጮኻል፡፡ የሐዋ ሥራ 4፥13-21፤1ዮሐ 1፥1-2 ፤ 2ቆሮ 6፥ 4-10


 

ወንጌል ዘማቴዎስ ፳፭፥፩፬-፴

      ጌታችን ባስተማረው በዚህ ማለፊያ ምሳሌ የሰው ዘርን በሁለት ወገን ከፍሏቸዋል፡፡ ገብር ሔር(መልካም አገልጋይ) እና ገብር ሀካይ(ሐኬተኛ አገልጋይ)፡፡

      በምሳሌው የተጠቀሰው ባለጠጋ ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡ ባሮቹን ጠርቶ ከገንዘቡ ሰጣቸው እንዲሰጣቸው አልጠየቁትም፤አልደከሙም ዋጋም አልከፈሉም፡፡ በዚህ ዓለም ያለድካም ያለደጅ ጥናት ያለዋጋ ምን ልናገኝ እንችላለን? አርሱ ግን የባህሪይ ገንዘቡ የሆነ መልካምነትን እውቀትን ህይወትን ሁሉ እንዲሁ በለጋስነቱ ብቻ ያለዋጋ ሰጠን፡፡ለጋስነቱን መዘከር ቸርነቱንም ማድነቅ የሚቻለው ምን ህሊና ነው!

     ሕይወት፣እውቀት፣ሰውነት(ሕዋሳት)፣ጊዜ፣ዕድሜ፣ሰላም፣ክህሎት፣ወዘተ…ለአዳም ዘር ሁሉ የተሰጠ የለጋስነቱ በረከት ናቸው፡፡ ይህን ከሰጠን በኋላ ወደሌላ ሀገር ሄደ ማለቱ ነፃ ፈቃድን ሰጠን፡፡ ለመሥራትም ወይም ላለመሥራት ለማትረፍ ወይም ለመስነፍ ምርጫው የራስ ነው፡፡ አስገድዶ አያሠራም፡፡ኋላም የሚያስፈርድብን በነፃ ፍቃዳችን የሠራነው ሥራ ነው፡፡

     ለጋስነቱ ያሰደነቃቸው ተመልሶ መጥቶም እንደሚቆጣጠራቸው ያልተጠራጠሩ እነርሱ አምኖ በሠጣቸው ለማትረፍ ተግተው ተስማሩ፡፡ ደከሙ ድካማቸው ፍሬ አስገኘላቸው፡፡በተሠጣቸው እኩል ማትረፍ እንዴት ያለ ትጋት ነው?

    ለጋሱ ጌታ እንደተጠበቀው መጣና ተቆጣጠራቸው ተግተው ያተረፉትን ሥራቸውን አስታወቁ፡፡ እርሱ በሰጣቸው ሌላ ማንም ሊሰጣቸው በማይችለው ጸጋ ተጠቅመው ለወገኖቻቸው የሚበጅ ሥራ በመሥራታቸው ተመሰገኑ፡፡ እርሱ በፍቅሩ መልካም የሆነውን ሁሉ እንደሠጣቸው፤እነርሱም ለሌሎች መልካም በማድረግ ፍቅራቸውን ገለጡ፡፡ በጥቂቱ ስለታመኑ በበዙ እንደሚሾሙ ተባለላቸው፡፡

     በምድር ታምነዋልና በሰማያት ይሾማሉ፡፡በጊዜያዊው ታምነዋልና በዘላለማዊው ይሾማሉ፡፡ በውሱን እውቀት ታምነዋልና በፍፁም እውቀት ይሾማሉ፡፡ ክርስቲያኖች ባለን በጥቂቱ እንታመን፡፡ በምዕመንነት የታመነ በዲቁና፣በዲቁና የታመነ በቅስና፤ በቅስና የታመነ በጵጵስና መሾሙ አይቀሬ ነው፡፡

     ከተግባረ ዕለት፤ከትምህርት ከእንቅልፍ ጥቂት ጊዜ አስተርፈን የሚበጅ ሥራ ለመሥራት ብንታመን አብዝተን መልካም የምንሠራበት የበዛ ጊዜ ይሠጠናል፡፡

    አሥራት በማውጣት ብንታመን ስስትን አጥፍቶ የበለጠ የትሩፋትን ሥራ በምንሠራበት ሁኔታ ይሾመናል፡፡

     በድንግልና ዘመን ብንታመን በትዳር ወይም በምንኩስና ዘመናችን በታላቅ ክብር ይሾመናል፡፡ ወዘተ…

     በለጋሱ ጌታ ለትጉህ አገልጋይ የተሠጠው ዋጋ የሚያስደንቅ ነው ወደ ጌታህ ደስታ ግባ በማለት ከእርሱ ጋር አብሮ እንዲኖር የተሠጠውን ክብር አብስሮታል፡፡


 

- ሐኬተኛው አገልጋይ ግን የተሠጠውን ጸጋ ዋጋ ሳይሠጠው ለስንፍናውም ምክንያት እንኳ በቅጡ ሳያዘጋጅ ቆየ፡፡ ጌታው ሲጠይቀው የሰጠው መልስ ምን ያህል ደካማ መሆኑን የገለጠ ነው፡፡

ጌታ ሆይ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ መሆንህን አውቃለሁና ፈራሁ ስለዚህ መክሊትህን ወሰጄ ከምድር በታች ቀበርኩት አሁንም እነሆ መክሊትህ፤

        ይህ ሰው ስንፍናውን በምክኒያት ሊደብቅ ቢሞክርም አልሆነለትም፡፡ የልቡናው ክፋትም በለጋስነት የሚታወቀውን ጌታን ጨካኝ ብሎ በመጥራቱ ታወቀ፡፡ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበት የምትሠበስብ ማለት ጌትነቱን ሁሉን የያዘ ፣ሁሉን ያስገኘ ፣በሁሉ ላይ የሠለጠነ መሆኑን መካድ ነው፡፡ ቢያንስ እሱን የተቆጣጠረው በሠጠው ላይ ነው፡፡ ይህም ፍትሕ ርትዕ ዙፋኑ ሞገስ እንደሆነ ያሳያል፡፡

       ምንጊዜም የሚጠበቅባቸውን መወጣት የማይችሉ ሰዎች ስንፍናቸውን ለመሸፈን የሚጥሩት በቅደስናው የተፈራ በሆነ በሠራዊት ጌታ ላይ ያልተገባ ንግግር በመናገር ነው፡፡ ፍርሃታቸው በሰው ፊት አንዳይታወቅ መደበቂያቸው ያልተገራ አንደበታቸው ነው፡፡ በልዑሉ ላይ የፌዝ ቃል ካልተናገሩ አዋቂ የሆኑ ቅዱሱን ካልተገዳደሩ የተፈላሰፉ የማይመስላቸው የልቅነት አቀንቃኞች ብዙ ናቸው፡፡ አንዲህ ያሉት ተሳዳቢዎች፣ፈሪዎች፣ሐኬተኞች የእግዚአብሔርን መንግስት አይወርሱም፡፡የሚያደምጣቸው ጽሑፋቸውንም  የሚያነብ ሁሉ በክፉ መርዝ ይያዛል በጥፋት ሥራቸውም ይተባበራል፡፡ ስድብና ልዑሉን መገዳደር ከዲያቢሎስ መሆኑን እናውቃለን፡፡

ኢዮብ ፈተናው ሲበረታበት ሰይጣን በሚስቱ አድሮ የተናገረው “እግዚአብሔርን ስደብና ሙት ”በማለት ነው መጽሐፈ ራዕይም “አውሬው እግዚአብሔርንና ስሙን ማደሪያውንና በሰማይ የሚያድሩትን ይሰድብ ዘንድ አፍ ተሰጠው” ተብሎ ተጽፏል ኢዮብ 2፥7-10፤ራዕ 13፥5-6

      ይህ ሀኬተኛ ባሪያ መክሊቱን በምድር ውስጥ እንደቀበረ ስንቶች እንሆን የተሠጠንን ጸጋ ከምድራዊ ጉዳያችን ይልቅ ትኩረትና ቅድሚያ ባለመስጠት ያጠፋን፡፡ የሚያሳዝነው ዛሬ ህይወታችንን፣ጊዜያችንን፣እውቀታችን፣ገንዘባችን ወዘተ…ለእግዚአብሔር እንዳንሰጥ ተሸንፈናል፡፡ ምክኒያቱም እነኚህን ሁሉ ከተወሰዱብን ቆይተዋል፡፡ በህይወታችን በጊዜአችን በእውቀታችን፣በገንዘባችን ወዘተ…የሚያዝበት ሌላ ነው፡፡ “System” የሚባል ሠንሠለት ጠፍንጎናል፡፡ነፃ ነኝ የምንል ባርያ ሆነናል ለፈጠረን ሳይሆን ለፈጠርነው ለቀደመን ሳይሆን ለቀደምነው እኛ ህልው ለሆንበት ሳይሆን በእኛ ህልውና ላገኘው ተገዝተናል፡፡ ይህን ቀንበር ሰብረን ስንወጣ ብቻ ነው የኛ የሆነውን ብቻ ሳይሆን ራሳችንን መስጠት የምንችለው፡፡ በምድር የቀበርነው መክሊት ሳይሆን በምድራዊ ሀሳብ የተቀበርን እኛ ትንሣኤ ያስፈልገናል፡፡ ፍፁም የሆነ የለውጥ ትንሣኤ የነፃነት ትንሣኤ በራስ የማዘዝ ትንሣኤ፣ የፈቀድነውን ብቻ የማድረግ ትንሣኤ ያሻናል!!!

    ይህ የወንጌል ክፍል በገብር ሔር /በመልካም አገልጋይ/ መሰየሙም የተገባ ነው፡፡ ክፉዎች ስም የላቸውምና፡፡ ለአርአያነት አይበቁምና ሰሙን ሊያስጠራበት ይችል የነበረበትን መክሊት በምድር ውስጥ ቀብሯልና የርሱም ስም በክፋትና በሀኬተኛነት ውስጥ ተቀብሮ ቀርቷል፡፡

ለመልካሙ አገልጋይ ግን የክፉው ዕድል/ድርሻ/ ጭምር ተወስዶ ተጨምሮለታል መልካሞች በጸጋ ለይ ጸጋ በሀብት ላይ ሀብት፣በክብር ላይ ክብር ቢጨመርላቸው ከራሳቸው አልፈው ለሌሎችም ይተርፋሉና፡፡

ይቆየን ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

ቀሲስ ታምራት ውቤ ዘሰአሊተ ምህረት

 

Read more...

ደብረዘይት

በስመ  አብ  ወወልድ  ወመንፈስ ቅዱስ  አሐዱ  አምላክ  አሜን!

የቀጠለ...

፭.ደብረዘይት፡- በዚህ ዕለት በቤተክርስቲያን ነገረ ምፅዓቱ ይታሰባል፡፡ ደብረዘይት ይህንኑ እውነታ ጌታ ለሐዋርያት ያስታወቀበት ተራራ ነው፡፡ ዳግመኛም መምጣቱ በዚሁ ተራራ እንደሆነ ይታመናል፡፡

ምስባክ፡- እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመፅዕ

        ወአምላክነሂ አያረምም

        እሳት ይነድድ ቅድሜሁ

ትርጉም፡- እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል

        አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም

        እሳት በፊቱ ይቃጠላል      መዝ ፵፱፥፪

 

- ይህ ሀይለ ቃል ለቀዳማዊውም ለዳግም ምፅዓቱም ይነገራል፡፡

- በቀዳማዊ ምፅዓቱ ግልጥ ሆኖ ይመጣል ሲል፤ በባህርዩ የማይታይ የማይዳሰስ ሲሆን ከእመቤታችን በነሣው ሥጋ የሚታይ የሚዳሰስ ሆኖ ምጣቱን ሲያጠይቅ ነው፡፡ እሳት ይነዳል ማለቱ አልመለስ ካሉ ፈርዶ የሚያጠፋበት ሥልጣኑ የባህርዩ መሆኑን ያሳያል፡፡ ማቴ 23

- ለደዳግም ምፅዓቱ ግልጥ ሆኖ ይመጣል ሲል፤ በክበበ ትስብዕት በግርማ መለኮት የሚመጣ መሆኑን ነው፡፡ ሲመጣም ሁሉ ተካክሎ ያየዋል፡፡ ላንዱ ቅርብ ላንዱ ሩቅ አይሆንም፡፡ አንዱ ከፊት ሌላው ከኋላ አንዱ ከቀኝ ሌላው ከግራ በኩል ሆኜ አየሁት አይልም ሁሉ በእኩል ርቀት ለሁሉ በፊታቸው ይታያቸዋል፡፡ ይህም ግርማ መለኮትን ወይም ምሉዕነቱን ያሳያል፡፡ ሲመጣም ጻድቃን ኃጥአን ፣ያመኑ ያላመኑ ሁለ ያዩታል፡፡

ዝምም አይልም ማለቱ ጻድቃንን ንዐ ኀቤየ(ወደኔ ኑ) ይጠራል፡፡ ኃጥአንን (ሑሩ እምኔን) ከእኔ ሂዱ ብሎ ሲያሰናብት ይሰማልና ነው፡፡ እሳት በፉቱ ይቀጣጠላል የተባለ ፍርዱ ነው፡፡

ወገኖቼ ክርስቶስ በእርግጥ ይመጣል፡፡ በእድሜያችን ላይ በቸርነቱ የሚጨመሩልን ቀናት ዕለተ ሞታችንን እንድንዘነጋ እንደሚያደርጉን፤ዕለተ ምፅዐትንም የወራት መበርከት የዘመናት መርዘም እንድንዘነጋው አድርጎናል፡፡ ህመም፣የዘመድ የወዳጅ መርዶ፣ ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋ ዜና ሁሉ እኛ ብንረሳውም ሞት እንደማይረሳን ማስታወሻ እንደሆኑ ዳግመኛ ምፅዓቱን እንዳንዘነጋ የተተውልን ምልክቶች አሉ፡፡ እነሆ፤-

ወንጌል ዘማቴዎስ ፳፬፥ ፩-ፍፃሜ፡-  በዙህ ምዕራፍ የተጠቀሱትን ሁሉ ለማብራራት ጊዜ ያጥርብኛል፡፡ ዋና ዋናዎቹን አጠር አድርገን እንመልከት፡፡

ሐዋርያት በደብረዘይት ሁለት ዓበይት ጥያቄዎች ጠይቀውታል፡፡

፩. ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ አይቀርም ብሎቸው ነበርና በዚያ አስደናቂ ቤተመቅደስ ላይ ይህ መቼ እንደሚፈፀም ማወቅ ፈልገው ነበር፡፡ ይህም በ70ዓ.ም በጥጦስ ዘመን ሆኗል፡፡ ጌታ በቤተመቅደሱ ላይ የተናገረው ፈጥኖ መድረሱ ላላውም በጊዜው ጊዜ መፈፀሙ የማይቀር መሆኑን ያስረግጣል፡፡

፪.ዳግመኛ መምጣቱ መቼ እንደሚሆን፡-

ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? ሐዋርያት በተለያየ ጊዜ ግለሰባዊ ጥያቄዎች እየጠየቁ ከጌታችን ዘንድ ተቀባይነት ባለማግኘታቸው በአሁኑ አጠያየቃቸው ላይ ጥንቃቄ ወስደዋል፡፡ አሁንም ግን “መቼ” የምትልውን ጥያቄ ጌታችን በተለመደው የማይመረመር ጥበቡ አልፏታል፡፡ ቀኑን ቆጥሮ ጊዜውን ሠፍሮ መናገሩ ፍጡራኑን ለሁከት ለጭንቀት ቢዳርግ እንጂ አይጠቅምምና፤አንድም እውነተኛ ወዳጅ ከአስመሳዩ(ከግብዙ) ይለይበታልና፤አንድም ሰው ከዕለተ ሞቱ ይልቅ ለዳግም ምፅዓቱ ትኩረት በመስጠት ከዕለቲቱ በብዙ ዘመናት የሚርቁት በኃጢአት ተዘፍቀው በበደል ተገርኝተው በሞቱ ነበር፡፡ በዳግም ምፅዓት ይዘን የምንቀርበው በሞታችን ጊዜ የነበረንን ነውና እንዳይጎዱ ቀኒቱን ሠወራት፡፡ ከሞት በኋላ ክፉም ሆነ በጎ ለመሥራት፤ጻድቅም ሆነ ኃጥዕ ለመሆን፤ለማመንም ሆነ ለመካድ አይቻልምና፡፡ማቴ 24፥36 

ከዚያ ይልቅ ጌታችን የወደደው ምልክቶቹን መንገር ነው፡፡ ምልክቶቹ በጥቅል ሲታዩ በሁለት መክፈል ይቻላል፡፡

ሀ. ሥጋዊ መከራዎች፡- ረሃብ፣ቸነፈር፣ጦርነት፣የተፈጥሮ አደጋዎች፣መንግስት በመንግስት ሕዝብም በሕዝብ ላይ መነሣት ወዘተ…በሥጋ ላይ የሚመጡ መከራዎች ነገር ግን መንፈሳዊነትም ጭምር የሚፈተንባቸው ናቸው፡፡ የሆነው ሁሉ ሊሆን ግድ ነውና ከመማረር ይልቅ ቀናቱ እንዲያጥሩ መፀለይ፡፡ ሌሎች በመከራው ተማረው ከሃይማኖት እንዳይወጡ በክፉ ምግባር እንዳይለወጡ መምከር ማስተማር የመንፈሳዊነት መገለጫ ነው፡፡ በጦርነት ውስጥ ምህረት፣በረሃብ ወቅት ተካፍሎ መብላት ፤በቸነፈር የሞት ጥላ ውስጥ መራራት በእግዚአብሔር ሰዎች ላይ የታየና የሚጠበቅም ነው፡፡

ለ. መንፈሳዊ ውጊያዎችን ይህም ዲያቢሎስ የክርስቶስ የሆኑትን ርትዕት ከሆነችው መንገድ ለማውጣት የሚከፍተው ነው፡፡ በዋናነት ከተጠቀሱት “እኔ ክርስቶስ ነኝ” እያለ በስሙ የሚመጡ እንዳሉና ሀሰተኞችም ነቢያትና መምህራንም እንደሚነሱ የተናገረው ነው፡፡ ይህም በየዘመናቱ ተፈፅሟል፡፡ ዛሬም አለ ነገ ይብስ ይመጣል፡፡ የዛሬ መልካምነቱ ከነገ የተሻለ መሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ የሚብስውን መጠበቅ ማስተዋል ነው፡፡ መጽሀፍ ቢቻላቸው “የተመረጡትን እስኪያስቱ ድረስ” ማለቱ ስህተቱ ምን ያህል በከፋ ደረጃ እንደሚመጣ ያሳያል፡፡

ነገር ከመራን ዘንድ ዛሬም በአዱስ አበባ ሀሰተኞች መምህራን ነቢዩ ኤልያስ መጥቷል እያሉ ህዝቡን ማደናገራቸው የዚሁ እውነታ አንዱ መገለጫ ነው፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ብቻውን ሳይሆን ከነቢዩ ሄኖክ ጋር እንደሚመጣ በኢየሩሳሌም አንደሚገለጡ ከሐሳዊው መሲህም ጋር ብርቱ ትግል አድርገውና ሀሰተኛነቱን ገልጠው ሕዝበ እግዚአብሔርን ካፅናኑ በኋላ በሰማዕትነት እንደሚሞቱ እናምናለን፡፡ ራዕይ 11፥1-13

ዛሬ መጥቷል የሚሉ ሀሰተኞች በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነትን በቀላሉ ለማግኘት ታዋቂ አርቲስቶችና ግለሰቦችን ተጠቅመዋል፡፡ ነገ በሥጋ የሚጠብቃቸው ኃፍረት በነፍስ የሚያገኛቸው ሞት እያስጨነቀን ነብዩ ኤልያስ በእንዱህ ዓይነት ሁኔታ ይልቁም በአዱስ አበባ እንደማይመጣ ለመናገር የምናውቀው የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ያሰገድደናል፡፡

ስለ ስሙ የተጠላን እንደምንሆንም ሌላ ምልክት ተሰጥቶናል፡፡ ማንም ሰው መጠላትን አይፈልግም፡፡መጠላት መገፋት፣ የመገለል፣ ያለመፈለግ፣ የብቸኝነት፣ ስሜት ውስጥ ስለሚከተን በራሳችን እርግጠኞች ወዳለመሆንም ጭምር ይወስደናል፡፡ ይህ ደግሞ ተስፋ ወደመቁረጥ ራስን ወደመጥላት ወይም በአንፃሩ ሌሎችን ወደመጥላትና ወደ መበቀል ይወስደናል ውጤቱም የከፋ ነው፡፡

እነሆ የክርስትና በረከት በዚህች ዓለም የክርስቶስ ተከታይ መሆን የሚያተርፍልን ነገር ቢኖር መገፋትን፤ መገረፍን፤ በወኅኒ መጣልን፣ በሰይፍ ተመትሮ በእሳት ተቃጥሎ መሞትን ወዘተ…ነው፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ የሚጠብቃቸው በረከት ይሄ ነው፡፡ ክርስቲያኖች በዚህ አልፈዋል፤ እኛም ክርስቲያኖች ከሆን በዚህ ማለፍ የሚጠበቅ እውነታ ነው፡፡ ወዳጄ ሆይ! ክርስቲያን በመሆንህ በዚህ ዓለም የምትጠብቀው ምንድር ነው? የተደላደለ ህይወት፣ ከበሬታ ሥፍራ፣ ከሁሉ በላይ መሆን…ምን? ፡፡ ከስህተት ተጠበቁ! ከክርስቶስ ጋር ቃልኪዲን ያደረግነው በክብር ሳይሆን በውርደት፣ በድሎት ያይደለ በመከራ፤ በመወደድ ሳይሆን በመጠላት፣ በህይወት ለመቆየት ያይደለ ስለ እውነት ለመሞት በተኩላዎች መካከል እንደበጎች ልንኖር ነው፡፡

ይህን የምንናገረው ያልመጣን መከራ ለመጥራት ሳይሆን ሲመጣ ክርስቶስ እንዴት ይህን ይፈቅዳል? ብለን እንዳንሰናከል ለማፅናት ነው፡፡ እርሱ የሆነውን አስቡ፤ እናቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እርሱን አዝላ በውሃ ጥምና፣ በረሃብ፤ በወንበዴዎችና በወታደሮች ፍርሃት የደረሰባትን አስቡ፡፡ ሐዋርያት ነቢያት ጻድቃን ሰማዕታት ካህናት መነኮሳት የደረሰባቸውን አስቡ፡፡ የእነርሱ ወገኖች ከሆን በእነርሱ የደረሰ ይደርስብናል፡፡ ዮሐ 15፥18-24፣ዮሐ 16፥33 ማቴ10፥16-23፣ሮማ8፥35-36፤ 1ቆሮ4፥11-13 

- ሌላው የተሰጠው ምልክት "ለአሕዛብ ምስክር ይሆን ዘንድ ይህ የመንግስት ወንጌሌ በአለም ሁሉ ይሰበካል" የሚል ነው፡፡

 ወንጌል ስለሁለት ምክንያት ይሰበካል፡፡ ለጽድቅና ለፍርድ አምነው ለሚጠቀሙበት በቃሉ ለሚኖሩ በወንጌል የዘላለም ህይወትን እንደሚያገኙ የተረጋገጠ ነው፡፡ በአንጻሩ ለራሳቸው ፍልስፍና የሚመቻቸውን ሃሳብ ለመምረጥ፤ ለዓለማዊ ድርሰታቸው ወግ ማሳመሪያ ቃላትንና ይትበሃሎችን ለመቃረም የሚነቅፈበትን ነገር ለማግኘት ወይም ልባቸውን ሳይከፍቱ በቸልታ የሚያነቡ ሁሉ ለፍርድ ምስክር ይሆንባቸው ዘንድ ያነባሉ፡፡  ሳይኖሩበትም ላይኖሩበትም በአጋጣሚ በወንጌል ላይ የተሾሙም ሁሉ ለፍርድ ያነቡታል፡፡

አህዛብ የሚለው በመጽሐፍ ቅዱስ በሁለት ይፈታል፡፡ የተለያየ ቋንቋ የሆኑትን ሕዝብ ሲያበዛው (plural) እና በክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅነት ያላመኑ አረማውያንን (ኢ-ጥሙቃንን) አህዛብ ይላቸዋል፡፡ ዛሬ አብዛኛው ማህበረሰብ ሙስሊም (ኢ-ጥሙቅ) በሆነባቸው አገሮች እንኳ ወንጌል በራሳቸው ሼኮች እየተሰበከ ነው፡፡ መድረሳዎቻቸው የቁርዓን መቅሪያ ብቻ ሳይሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ማጥኛ ጭምር ከሆኑ ሰነባብተዋል፡፡  ለዚህ ደግሞ ጉልህ ማስረጃ የሚሆኑን እንደ ዛኪር ናይክ እና አህመድ ዲዳት ያሉት የማያውቁት አገረ ገብተው የሚዛብሩ የዲያብሎስ መልዕክተኞች ናቸው፡፡

በኢትዮጵያ ካለው EBS TV ጀምሮ በዓለም ባላቸው ቻናሎች ሁሉ ለተከታተለ ሰው ዛሬ የሚሰብኩት ከመሀመድ ይልቅ ክርስቶስን ከቁርዓን ይልቅ መጽፈፍ ቅዱስን ነው፡፡ ምንም እንኳ በአሉታዊ መልኩ ሊያቀርቡት ቢሞክሩም ትንቢቱ ግን ተፈጽሞባቸዋል፡፡ አንድ ቀን እውነቱ ግልጽ ይሆናል መስቀል በጨረቃ ላይ ይቆማል ለእስማኤሌም ወንጌሌ ይሰበካል! እንፀልያለን !!! ያ ህዝብ ነጻ እንዲወጣና በጨለማ በጨረቃ ብርሃን በድንግዝግዝ ከሚያይ አጥርቶ ወደሚያይበት ወደ እውተኛው የጽድቅ ፀሐይ ብርሃን እንዲመጣ አንፀልያለን ኮከቡ እየማራ ቤተልሔም እንዲያደርሳቸውና ህፃኑን አሳይቶ ድንጋይ ማምለክን እንዲያስረሳቸው፡፡ አሜን! ለይኩን ለይኩን!

- በመጨረሻም ጌታችን ኢየሱስ  ክርስቶስ "ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ ጀምሮ ያልሆነ መከራ እንደሚሆን ካሳሰበ በኋላ ቀኖቹ ግን ስለተመረጡ ሰዎች ሲባል ያጥራሉ፡፡ ያ ባይሆንስ ሥጋ የለበሰ ሁሉ ባልዳነም ነበር” በማለት የመከራውን ጽናት ገልጾታል፡፡ ያለ ተስፋ ግን አልተወንም ቅዱስ እግዚአብሔር ለመንግስቱ በልጁ ደም ስለዋጃቸው በእውነትና በመንፈስ ስለሚገዘት ቅደሳን ሲል ቀኖቹን ያሳጥራቸዋል፡፡

ዱያብሎስ ዛሬ እንኳን ለወንጌሌ ቸልተኞች የሆኑትን ቀርቶ በመንፈሳዊ ህይወት በመጋደል ላይ ያሉትን እንኳን በረቂቅ ስጋዊ ወጥመዶች ስልጣን፣ ገንዘብ፣ ዝና ወዘተ . . . እየሳበ ንቀው ጠልተውት ወደ ተውት አለም መልሷቸዋል፡፡

የንጽህናና የቅድስና ህይወት በተለያዩ የማስመሰያ ምክንያቶች ተሸራሽሯል፡፡ ምላስ ጸድቃ ነፍስ ረክሳለች፡፡ አባቶቻችን የነፍሳቸው ቅድስናና ክብር ለሥጋቸው የሥጋቸው ለልብሳቸው፣ ለመቋሚያቸው ወዘተ . . . ተረፈ ፡፡ እነሱ ከክፉው ሠራዊት ጋር ላለባቸው ሰልፍ የለበሱት ልብስ እኛ በከንቱ ለመሞገስ ለበስነው፡፡ ልብሱ በእነሱ ከበረ እኛ በልብሱ ተከበርን፡፡ 

ይህ ሁለ ተንኮል ዱያብሎስ የመከራ ዘመን እንዲያጥር ምክንያት የሚሆኑ ምርጦች እንዳይኖሩ ለማድረግ ነው፡፡ ቅዱሳን ዋዕየ መከራን የሚከልሉ ደመናዎች፤ የደከመ ጉልበት የሚያፀኑ ምርኩዝች ናቸውና፡፡ ያለ ቅዱሳን ይህቺን ዓለምና የእኛን ህይወት ማሰብ ከባድ ነው፡፡ በከተማይቱ አስር ጻድቃን ቢኖሩ እምራለሁ ያለ እርሱ በፊቱ የሚቆም ከጠፊ  ሊሆን የሚችለውን መከራ በሰው አእምሮ ከመታሰብ በላይ ነው፡፡ ሰዶምና ገሞራን ይዘክሯል፡፡ ታላቁ ተስፋችን የአምላካችን ቸርነቱና የቅዱሳን ፀሎት ነው፡፡

የሥጋ ፈተና ይፈፀማል የምድርም ሥርዓት ያልፋል፡፡ ጠላቶቹ በዘላለም ጉስቁልና የሚኖሩበት የገሃነም ጨለማ ይገለጣል፡፡ ወዲጆቹ እንደተስፋ ቃሉ የጠበቋት የበጉ ከተማ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት በክብር ትታያለች፡፡የልባቸው ናፍቆት የነፍሳቸው ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እኔ ኑ ብሎ ሲጠራቸው ለዘላለም ደስታ ወደ ከተማይቱ ይገባሉ፡፡ ከእኔ ሂዱ የተባሉ ኃጥአንም ወደ ዘላለም ጉስቁልና ይወርዲሉ፡፡ ምልጃ የለም ልመናም የለም መስዋዕት መሠዋት በንስሐም መማለል የለም፡፡“ አልቦ ምህረት በጊዜ ፍትህ” እንዱል ምህረት ይከለከላልና፡፡

 በገሃነም ያለውን ሥቃይ በኢየሩሳሌም ሰማያዊት የሚፈሰውንም ደስታ መግለጥ የሚቻለው አንደበት የለም በጊዜው ጊዜ ሲገለጥ ከማየት በቀር ፡፡ማቴ 25፥31-46፣ ራዕይ 8፥13-17እና ራዕይ21፥1-4

በምድር ያለ ግፍ ጢሱ ያፈናቸው፤ የኃጢአት ክርፋት የገለማቸው ጊዜያቸው እስኪደርስ በዚህ የበደል ዓለም እንዲኖሩ ግድ የሆነባቸው ቅዱሳን ያቺን ዓለም ይናፍቃሉ፡፡

ሐዋርያት አዕማዶቿ አበው ደጀፎቿ አማናዊው በግ ኢየሱስ ክርስቶስ ንጉሷና ብርሃኗ የሆነችውን፤ ጽድቅና እውነት ብቻ የሚፈፀምባት የአምላካቸው ድንኳኑ የሚተከልባት ዙፋኑ የሚዘረጋባትን ብርህት ዓለም ይናፍቃሉ፡፡ ዛሬ ከሩቅ ያዩአታል ይሳለሟታል በመዓዛዋ ተመስጠው በናፍቆቷ አንብተው ዓለምን ይንቁባታል፡ ይቃትታሉ፣ ይጮሃሉ፣ ይጣራሉ "ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና!" እያሉ፡፡ ራዕይ 21፥9-14 ፣ ራዕይ 22፥20 ፣ 1ቆሮ 16፥22

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

2008 ዓ.ም

 

 

Read more...

የመጋቢት ወር ልምምድ

በሃይማኖት /እምነት/ መኖር
ሃይማኖታቸን ከልማድ ፣ ከቸልተኝነት ፣ ከተጽኖ ነፃ መሆኑን መመርመርና መለማመድ
ከሃይማኖታችን በምድር ምን በሰማይ ምን እንደምናገኝ መመርመር
ለሃይማኖታችን ምን እንዳደረግን መመርመር
የመንደገፍባቸውን ሌሎቸ ነገሮች ማስወገድ / ምሳሌ ፡- ሥራ ፣ ገንዘብ ፣ ወገን ፣እውቀት ወዘተ ……/

 

 
 
Read more...

የየካቲት ወር ልምምድ

ምኞትን መዋጋት
የሚያስፈልገንን ከምንፈልገው መለየት 
ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን መለማመድ / ደስታችንና ሃዘናችን ብማግኘትና በማጣት ላይ እንዳይወሰን 
መንፈሳዊ ምኞቶችን መለማመድና ማዳበር / የቅዱሳንን ሕይወት በማወቅ 
ዓለም ልትሰጠን የምትችለውን ፣ የአለምን መልኩአን፣በኅላም ኃላፊ መሆኗን መለየት 
 
 
Read more...

ጥር ወር ልምምድ

ራስን መሆን 
በይሉኘታ የምንሰራውን መጥፎ ነገር ማስወገድ 
ከሰው ጋር በመፎካከር የምናደርገውን ማስወገድ 
በእግዚአብሔርና በሰው ፊት የማስመሰልን ሕይወት ማስወገድ 
Read more...
Subscribe to this RSS feed

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ