Login
Main menu

Items filtered by date: June 2026

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል ስድስት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

እንኳን ለብርሃነ ልደቱና ጥምቀቱ አደረሳችሁ፡፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ዕረፍትም ረድኤትም በረከት ያሳድርብን አሜን!

ባለፉት ተከታታይ ትምህርታዊ ጹሑፎች አምላክ ልንለው የምንችለው አካል ሊያሟላ ስለሚገባው ባህርያት እያየን እዚህ ደርሰናል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ በሁሉ ሥፍራ የሚገኝ አምላክ ነው ስንል ምን ማለታችን ነው? የትኛውም ፍጡር በቦታ በጊዜና በሁኔታ የተወሰነ እንደሆነ የነገረ-መለኮት ሊቃውንትም ሆኑ የፍልስፍና ሊቃውንት ይስማሙበታል፡፡ በምድራውያንም ሆነ ለሰማያውያን ግዙፉንም ይሁኑ ረቂቃን ፍጥረታት በዚሁ የታጠሩ ናቸው፡፡

ሰማያውያን መላእክት እንኳ የልዑሉን ትዕዛዝ ለመፈፀም ሲተጉ አንዱን ሥፍራ ለቀው ወዳንዱ መሔድ ግድ ይላቸዋል፡፡ እንደሪቂቅነታቸው በረቂቅ ከተማ በሦስቱ ሰማያት ኢዮር፣ ራማና ኤረር ወስኖ አስፍሯቸዋል፡፡ ተልኳቸውን ከፈፀሙ በኃላ ወደዚሁ የመላእክት ከተማ ተመልሰው በምስጋና ይተጋሉ፡፡

ለልዑል እግዚአብሔር ግን እንዲህ አይደለም፡፡ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው እንደተናገረው     "ለመለኮት በታች ያለውን ለማንሳት ማጎንበስ ራስንም ማዘንበል ያለበት አይደለም በላይ ያለውን ያወርድ ዘንድ በፊትና በኋላ በቀኝና በግራ ያለውንም ለማቅረብ መዘዋወር የሚያሻው አይደለም፡፡ ሁሉ በእጁ የተያዘ ነው እንጂ" ቅዱስ ዳዊትም " ከመንፈስህ ወዴት እሔዳለሁ፤ ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ ወደ ሰማይ ብወጣ አንተ በዚያ አለህ፤ ወደ ውቅያኖስም ጥልቅ ብወርድም በዚያ ትገኛለህ፤ እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ ከአጽናፍ አጽናፍ ብበርም እጅህ በዚያ ትመራኛለች ቀኝህም ትይዘኛለች" በማለት ስለ ልዑል እግዚአብሔር በሁሉ መገኘት ዘምሯል፡፡ መዝ139፥7-10፤ ቅዳሴ ማርያም

ቤተመቅደስን ያነፀ ሰሎሞንም በጌታ እግዚአብሔር ፊት ሲፀልይ…"ሰማያትም ከሰማያትም በላይ ያለ ሰማይ ሊይዙህ አይችሉም፡፡ እንግዲያው እኔ የሠራሁት ቤት እንዴት ያንስ?..."በማለት ገልጾታል፡፡ 1ነገ 8፥27

በኢሳይያስም "ሰማይ ዙፋኔ ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት ለእኔ የምትሠሩልኝ ቤት እንዴት ያለ ነው? ሲል በሁሉ የመላ መሆኑን ገልጿል፡፡ ኢሳ66፡1፤ ማቴ 5፥34

በዘመኑ ፍፃሜ በመጽሐፍ ቅዱስ "በመጀመርያ ቃል ነበር፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበር፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበር ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለእርሱ አልሆነም" ተብሎ ልዕልናው ምልዓቱ ስፍሐቱ ከሀሊነቱ የተነገረለት አምላክ "ቃል ሥጋ ሆነ" ተብሎ ትህትናው ተገለጠ፡፡ ምልዓቱን ስፍሐቱን ሳይለቅ ባጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወሰነ፡፡ የሰውን አካልና ባህርይ በመንሳቱ በቦታ በጊዜና በሁኔታ የማይወስነው እርሱ በቦታ በጊዜና በሁኔታ ተወሰነ፡፡ ዮሐ1፥1-14

በቦታ ስንል ፤ በቤተልሔም ተወለደ፣ ወደ ግብፅ ተሰደደ፣ በናዝሬት አደገ፣ወደ ምኩራብ ገባ፣ ወደ  ኢየሩሳሌም ወጣ፣በቀራንዮ ተሰቀለ፣በጎሎጎታ ተቀበረ ወ.ዘ.ተ…ማለት ነው፡፡

በጊዜ ስንል፤ በ12 ዓመቱ ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፣ በ30ዘመን ተጠመቀ እርሱም ራሱ "ጊዜዬ ገና ነው" ብሎ እንደተናገረ የመሳሰሉትን ነው፡፡

በሁኔታዎች፤ ማለት ተፀነሰ፣ ተወለደ፣ ተሰደደ፣ ተራበ፣ተጠማ፣ ተገረፈ፣ ተሰቀለ፣ ሞተ ፣ ተቀበረ ወዘተ… ማለታችን ነው፡፡

ነገር ግን ምንም እንኳ ከላይ ለተጠቀሱት ነገሮች ተገዢ ባይሆንም በፈቃዱ በእውነት በእነዚህ ስር ሆነ፡፡  ያም ሆኖ ግን ለእኛ የለበሰውን ደከማ ሥጋ ብቻ ሳይሆን ኃያል አምላክነቱን ፣አላዋቂ ሥጋን የተዋሀደ ሁሉን አዋቂነቱ፣ ራሱን ባዶ በማድረጉ ውስጥ ያለ ባለጠግነቱን (ሁሉ የእርሱ ከእርሱ በእርሱ መሆኑን) በውሱንነት የተጋለጠ አለመወሰኑን ወዘተ…በሥራውና በቃሉ ገለጠለን፡፡

በማኅፀነ ማርያም ያለተከፍሎ በምልዓት እያለ ሊወሰን ከምልዓቱ አልጎደለም፡፡ በምሳሌ ፀሐይ በጠፈር ሰማይ ሆና ብርሃኗ ወደምድር ሲመጣ በፀሐይቷ ዘንድ በምልዓት አንዳለ ከእኛ ዓይን እንዲዋሃድ፤ ጨለማውን እንደሚገፍ የተሰወረውን እንደሚገልጥ የእርሱም እንዲሁ ነው፡፡ ከሦስተንቱ አልጎደለም  አራት ወደመሆንም አልተጨመረም፡፡ ይህንም በቃሉ ሲያስረግጥ…"ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ የለም ይኸውም በሰማይ ያለ የሰው ልጅ ነው" ብሏል፡፡ ዮሐ 3፥13 ይህን በተናገረበት ቅፅበት በኒቆዲሞስ ፊት ያለ እርሱ እንደምን በሰማይ ያለ የሰው ልጅ ነው ሊል ይችላል? ምልዓቱን(በሁሉ ቦታ መገኘቱን) ለመግለፅ ካልሆነ በቀር፡፡

ለሐዋርያትና በስሙ ላመን ክርስቲያኖች ሁሉ በገባልን ቃልም እንዲህ ብሏል፡-

ማቴ18፥20 …በስሜ ሁለትና ሦስት ባላችሁበት በመካከላችሁ እሆናለሁ፡፡

ማቴ28፥19… አባቴ አንደላከኝ እኔም እናንተን እልካችኋለሁ፡፡ ሂዱና አህዛብን በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ያዘዘኳችሁንም እያስተማራችሁ ደቀመዛሙርቴ አድርጓቸው፡፡ እነሆ እስከዓለም ፍፃሜ ከእናንተ ጋር ነኝ፡፡

ይልቁንም ቅዱስ ጳውሎስ ለቈላስዩስ ሰዎች በላከው መልዕክቱ " የመለኮቱ ሙላት በሥጋው ተገልጦ ይኖራል " እንዳለ በለበሰው ሥጋ በመለኮታዊ ሥልጣን በአባቱ ዙፋን በአባቱ ክብር ተቀምጦ ራቂቁንም ሆነ ግዙፉን ዓለም የሚታየውንም ሆነ የማይታየውን እንደሚገዛ እንዲሚጠብቅ እንደሚያስተዳድር ገልጿል፡፡ቆላ 2፥9

ዳግመኛም ሲመጣ በክበበ ትስብዕት በግርማ መለኮት ይመጣል፡፡ ይህም ማለት በክበበ ትስብዕት የተወጋ ጎኑ፣ የተቸነከሩ እጆቹ እግሮቹ እየታዩ ይመጣል፡፡ ምንም እንኳ በክበበ ትስብዕት ቢሆንም እነደ አምላክነቱ ሁሉ እኩል ያየዋል፡፡ በኋላ በቀኝ በግራ የሚሆን የለም አንዱ ቀርቦ አንዱ ርቆ አንዱ ከጀርባ አንዱ ከጎን ሆኖ አያያውም፡፡ ለሁሉ በእኩል ከፊቱ ሆኖ ይመለከተዋል አንጂ፡፡ ምን የአዳም ዘር በዝቶ እንደ እንድጽፍቀተ ሮማን ቢጨናነቅ ሁሉ በእኩል ርቀት በአንድ ዓይነት በፊቱ ያየዋል፡፡ ይህም ግዙፍ ሲሆን ረቂቅ ውሱን ሲሆን ምሉዕ አምላክ መሆኑን በተረዳ ነገር ያሳያል፡፡

ልዑል ሲሆን ሳለ ትሁት ሆኖ ራሱን በምንችለው መጠን የገለፀልን፤ ይወዳጀን ዘንድም ፍቃዱ የሆነ ጌትነቱን ፈጣሪነቱን የባህርይ አማላክነቱን አምነን እንመስክር ዘንድ የመረጠን የነገሥታት ንጉሥ የጌቶች ጌታ የአማልክት አምላክ የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ቸር ከሆነ ከሰማያዊ አባቱ አዳኝ ርኅሩኅ ከሆነ ከመንፈስ ቅዱስም ጋር ክብር ምስጋና ይግባው፡፡

ለዘለዓለሙ አሜን!

Read more...

ታሪከ አበው: አብርሃም

Download
Name
Play
Size
Duration
download
አብርሃም ክፍል 5
My Recording

80.5 MB
58:36 min
download
አብርሃም ክፍል 3

38.7 MB
56:23 min
download
አብርሃም ክፍል 2

59.1 MB
1:04:32 min
download
አብርሃም ክፍል 4
My Recording

129.2 MB
1:34:05 min
download
አብርሃም ክፍል 1

136.6 MB
59:42 min
download
አብርሃም ክፍል 6
My Recording

84.6 MB
1:01:38 min

Read more...

ሰማእትነት

Download
Name
Play
Size
Duration
download
Sema-etnet part2
My Recording

176.4 MB
2:08:26 min
download
Sema-etnet part1
My Recording

184.8 MB
2:14:34 min

Read more...

የሰኔ ወር ልምምድ

ዓቃቤ ሕዋሳት 
-ሕዋሳትን መጠበቅ መለማመድ /አንደበት ፣ዓይን ወዘተ 
-ለሕዋሳት የጽድቅ ሥራን ማስለመድ /ዝማሬ ፣ጸሎት፣ስግደት ወዘተ 
Read more...

ጰራቅሊጦስ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!

ጰራቅሊጦስ የሚለው ቃል የጽርዕ ሲሆን ‹‹የቅርብ ረዳት፤በአጠገብ ሆኖ የሚያፅናና የሚያረጋጋ›› የሚለውን ትርጉም ይሰጣል፡፡ይህ መጠሪያ በመጽሐፍ ቅዱስ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ከተጠራባቸው ስሞች አንዱ ነው፡፡

     ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ለዓለም ከገለጠና ምሥጢረ መንግሥትን ሦስት ዓመት ለሐዋርያት ሲያስተምር ከቆየ በኋላ ጊዜው እንደደረሰ አውቆ ለሐዋርያት ከእነርሱ ተለይቶ እንደሚሔድ ነግሯቸው ነበር፡፡ በእርግጥ ሐዋርያት ተላልፎ የመሠጠቱንና የሞቱን ነገር ደጋግመው ሲሰሙት የነበረ ቢሆንም የተቆረጠው ቀን መድረሱን ሲረዱ ግን ከፍተኛ ድንጋጤ ወደቀባቸው፡፡

     በዚህ ጊዜ ነው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ እሔዳለሁ ስላችሁ ደስ ሊላችሁ ይገባል፤እኔ ካልሔድኩ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና ያላቸው፡፡ ጌታችን የሐዋርያትን መደንገጥ ማዘንና መሸበር ሲያይ መንፈስ ቅዱስ ወደ እነርሱ የሚመጣው ሊያረጋጋቸውና ሊጽናናቸው መሆኑን አብስሯቸዋል፡፡ ያድርባችኋል በውስጣችሁም ይኖራል እርሱም ዓለም ሊቀበለውና ሊያውቀው የማይችል የእውነት መንፈስ ነው በማለትም አስረድቷቸዋል፡፡

     የክብር ጌታ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ነሥቶ ከተነሳ በኋላ

በ$ኛው ቀን ሲያርግ ‹‹አብ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ›› በማለት ተስፋን ሰጥቷቸው ሄዷል፡፡ ከአሥር ቀን በኋላም እንደ ቃሉ ተፈጽሟል፡፡ ሉቃ 24፥49

     መጀመሪያ በሐዋርያት ለጥቆም በምዕመናን ላይ መንፈስ ቅዱስ አደረባቸው ስንል ሀብቱ ጸጋው ኃይሉ ማለታችን እንጂ በአካል በእነርሱ አደረ ለማለት አይደለም፡፡ያደረባቸው ሰዎች በሚያሠራቸው ሥራ ተገልጠው ይታወቃሉ፡፡ መንፈስ ቅዱስየሚሠራው ሥራ የሚሰጠውም ኋይልና ጸጋ በዓለም ባለ የትኛውም ጥበብ፣ ሀብትና ሥልጣን ሊገኝ(ሊሠራ) ፈጽሞ የማይችል ነው፡፡

     ጌታ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ባደረባቸው ጊዜ ከብልየት ታደሱ በአዕምሮ ጎለመሱ፤ ፍሩሃን የነበሩ ጥቡዓን ሆኑ፡፡አንዲት ቋንቋ ብቻ ይናገሩ የነበሩ  ፸፩ቋንቋ ገለጠላቸው፡፡ መተርጉማን ስለምን ቋንቋው ፸፪ሆነቢሉ በጊዜው በዓለም ይነገር የነበረ ቋንቋ(ልሳን) ይኸው ነበርና ለዓለም ሁሉ ወንጌል መንግሥትን ይገልጡ ዘንድ ፈቃዱ መሆኑን ሊያጠይቅ ነው ይላሉ፡፡ የሐዋ.ሥራ 2፥1-ፍጻሜ

     ከዚህም በተጨማሪ መጻሕፍትን ከገበታ እስከ ገበታ አወቁ ምሥጢር ተገለጠላቸው፤ ትንቢተ ነቢያትን እነርሳቸውን መስለውና ተካክለው ተረዷቸው ተረጎሟቸው አመሰጠሯቸው፡፡ጌታችን የትምህርታቸውን(የቃላቸውን)ደገኛነትም በሚከተሏቸው የተለያዩ ምልክቶች አጸናላቸው፡፡ ያመኑትን ድውያንን ፈወሱ ሙታንን አነሱ፡፡ለወንጌል እንቅፋት የሆኑባቸውን በተግሳጽ በመቅሰፍት ከመንገድ አስወገዱ፡፡ እንግዲህ ይህ ሁሉ ሀብት ጸጋና ኃይል በየትኛውም ምድራዊ ኃይል፣ ሥልጣን፣ጥበብና ብልጥግና ሊገኝ የማይችል ከላይ(ከአርያም)ለመሆኑ ማረጋገጫ ነው፡፡ ማር 16፥17፤የሐዋ.ሥራ 3-6፤የሐዋ.ሥራ 13፥7-12

     ለመግቢያ ያህል ይህን ካልን ጰራቅሊጦስ ማለት ምን ማለት ነው የሚለውን በዝርዝር ለማየት እንሞክራለን፡፡ ጰራቅሊጦስ ማለት፡-

1. መጽንዒ ወይም የሚያጸና ማለት ነው፡፡ሐዋርያት ወንጌል መንግሥትን ለመስበክ የወጡት መልእክታቸውን አሜን ወአሜን ብሎ ለመቀበል በናፍቆት ወደ ሚጠብቅ ሕዝብ አይደለም፡፡ ይልቁንም በጥላቻ በተመረዙ አይሁድና በጣዖት አምልኮ በደነዘዙ አሕዛብ መካከል ነው፡፡

     የክርስትና አስተምህሮ በወቅቱ ከነበረው የዓለም ኅብረተሰብ ባህልና አኗኗር ጋር የብርሃንና የጨለማ ያህል መራራቅ ነበረው፡፡በመሆኑም አይሁድን ሥርዓተ ኦሪትን አሕዛብን ልማደ ጣዖትን ለማስጣል ሲወጡ ብዙ ግፍንና መከራን ተቀብለዋል፡፡ጌታችን እንዳላቸው ኃይልን ሳይቀበሉ ለስብከት ወጥተው ቢሆን ኖሮ መንፈስ ቅዱስ ባላደረበት ሰውነታቸው መከራ ቢያጸኑባቸው ፈጥነው ይክዱ ነበር፡፡ስለዚህ የሚመጣውን ለመቀበል መጨከን እንዲችሉ የሚያጸና መንፈስ ቅዱስ አድሮባቸዋል፡፡

     አበው መንፈስ ቅዱስ ስለምን በእሳት አምሳል ታያቸው የሚለውን ሲተረጉሙ፤በእሳት የተቃጠለ(እሳት የነካው)መሬት ለአዝርዕት ለአትክልት እንዲመች መንፈስ ቅዱስ ያደረበትም ሰውነት ለገድል ለትሩፋት የተመቸ ነው፡፡አንድም ሸክላ ሠሪ ሸክላ ሠርታ በእሳት ተኩሳ እንደምታጸናው መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰውነት ለገድል ለትሩፋት ጽኑ ነውና ይላሉ፡፡

     መንፈስ ቅዱስ ባያድርባቸው ኖሮ ነቢያት በትንቢት ሐዋርያት በስብከት፣ሰማዕታት በደም ጻድቃን በገዳም ፀንተው ለመገኘት ባልተቻላቸውም ነበር፡፡

2. መንጽሒ፡-የሚያነጻ ማለት ነው፡፡ሰው ኃጢአት ሢሠራ የእግዚአብሔርን ልጅ የሚመስለው መልኩ ይበላሻል ባህርዩ የጎሰቁላል ጠባዩም ያድፋል፡፡በሠራነው ተጸጽተን ንስሐ ገብተንና በካህኑ የተሰጠንን ቅኖና ፈጽመን ካህኑ ከሚያደርሰው ጸሎት ጀምሮ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እስከ መቀበል ድረስ የኃጢአት ሥርየታችን የሚከናወነው በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

እሳት ብረት ቢሉ ዝገቱን ወርቅ ቢሉ ዕድፉን አስወግዶ የቀደመ የተፈጥሮ ባህርያቸውን እንደሚያሲዛቸው እኛም በኃጢአት ምክንያት የጠፋ መልካችን ያደፈ ጠባያችን የጎሰቆለ ባህርያችን ነጽቶና ታድሶ ወደ ክቡር(ማንነቱ)የሚመለስ በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

     እመቤታችን በተለየ አካሉ አግዚአብሔር ወልድን ጸንሳ ለመውለድ እንድትችል ጥንት በአበው ባሕሪይ በማዕከል በማኅፀነ ሐና ኋላም በሕልውና ሳለች ንፅህት አድርጎ የጠበቃት ያዘጋጃት ያበቃት መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ያነጻ የከፈለ ያዋሀደ መንፈስ ቅዱስ ነው እንዲሉ ሊቃውንት፡፡

3. ናዛዚ፡- የሚያፅናና ማለት ነው፡፡ በዚህ መከራ በበዛበት ዓለም በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመንና በመልካም ሥራ በመትጋት በአብ ኅሊና ታስበው ያሉት በዚህ ዓለም በሚደርስባቸው መከራሲያዝኑና ሲተክዙ የሚያፅናናቸው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

     በመግቢያው እንዳየነው የሚያጽናና ስንል የቅርብ ረዳት የመንገዳችን ደጋፊ የነፍሳችንን ሲቃ አዳማጭ የማይለይ ታዳጊ ማለታችን እንጂ ተራ ደርሶ ሒያጅ አጽናኝ ማለት አይደለም፡፡በዓለም የሚወድቅብንን ሀዘንና ሰቆቃ ሁሉ ድል አንድንነሳው የሚያደርገን እርሱ የቅርብ አረጋጊ አጽናኛችን በመሆኑ ነው፡፡

     የቅዱሳን ሀዘን ራበኝ ጠማኝ ሀብት ንብረት ጠፋብኝ ወረት አነሰኝ ዘመድ ወገን ሞተብኝ ብለው አይደለም፡፡ ፍትሕ ሲጓደል ድሃ ሲበደል፤ እውነት ስትኮስስ ሀሰት ሲነግስ፤ የአዳም ዘር ፍርድ እንዳለ ዘንግቶ በኃጢአት በበደል ሲረክስ፤ ጻድቃንሲበደሉ ኃጥአን በምቾት በቅንጦት ሲደላደሉ ሲያዩ አምርረው ያዝናሉ፡፡ይልቁንም በቤተ እግዚአብሔር እውነተኞች መምህራን በግፍ ሲባረሩ መናፍቃንና ለመንጋው የማይራሩ ምንደኞች ሲከበሩ አምልኮተ እግዚአብሔር ሲጣስ ሥርዓት ሲፈርስ፤ ከጽድቅ ይልቅ የግብዝነት ካባ ሲደረብ ሲመለከቱ ልባቸው በሀዘን ነፍሳቸው በምሬት ይቆስላል፡፡

     በዚህ ጊዜ ጌታ መንፈስ ቅዱስ በማይመረመር ፍርዱ የደሀን ደም ሲበቀል ፍትሕን ሲተክል፤እውነትን ሲያነግስና ሀሰትን ሲደመስስ፤ በኃጢአት የከበሩ ሲዋረዱ ስለጽድቅ የተዋረዱት ሲከብሩ ፤ በኃጢአት በክህደት የተያዘውንም ሕዝብ በመጽሐፍት በመምህራን አንደበት መክሮና አስተምሮ ሲመልስ፤ በቤቱም እውነተኞቹን መምህራን አስነስቶ መናፍቃንና ምንደኞን ለይቶ አውጥቶ ሥርዓትንሲመልስ አምልኮተ እግዚአብሔር በግብዝነት ሳይሆን በእውነትና በመንፈስ ሲሆን ሲመለከቱ የቅዱሳን ልባቸው ይታደሳል ነፍሳቸው ይጽናናል፡፡ ይህም በዘመናት ሁሉ የታየ በቅዱሳት መጻሕፍትም ሆነ በታሪክ መጻሕፍት የተዘገበ ነው፡፡በፍርዱ ቅዱሳንን ያጽናናል ግፈኞችን ደግሞ እንደሥራቸው ጽዋቸውን ይግታቸዋል፡፡ የእመቤታችንንና የሐና እመ ሳሙኤልን ጸሎት ልብ ይሏል፡፡ ሉቃ 1፥46-ፍጻሜ፤ 1ኛ ሳሙ 2፥1-10

 


 

4. አራኃዊየሚከፍትማለት ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ ካልሆነ በቀር ኢየሱስን ጌታ(የሕያው እግዚብሔር ልጅ፤አምላክ ወልደ አምላክ ሊል የሚችል የለም፤ እንዳለ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የተገለጠ እርሱን ዓለማትን ካለመኖር ወደ መኖር የመጣ መጀመሪያውና መጨረሻው የሆነ አምላክ ብሎ ማመን በመንፈስ ቅዱስ ካልሆነ ከባድ ነው፡፡ 1ኛ ቆሮ 12፥3

     የተመሰገነው ሐዋርያ‹‹በወንጌል አላፍርም››ማለት ወረደ ተወለደ እንደ ሰው ተመላለሰ፤ ተገረፈ ተሰቀለ ሞተ ተነሳ ዐረገ ብዬ በማመንና በማስተማር አላፍርም ያለ ለዚህ ነው፡፡ሰዎች አምላክ ብለው በኅሊናቸው የሳሉትና የጌታችን ትሑት ሆኖ በመካከላችን መገለጥ በቀላሉ ለመቀበል የሚቸግር ነውና፡፡ ሮሜ 1፥16

     በሐዋርያት ሥራ ሐር ሻጭዋ ልድያ ሰለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ጳውሎስ የሚናገረውን ታዳምጥ ዘንድ ጌታ ልብዋን ከፈተላት ተብሎ የተጻፈ ለዚህ ነው፡፡ የሐዋ.  ሥራ 16÷14-15 የእግዚአብሄርን ቃል  ሰምተን መንፈሳዊ ፍሬ የማይታይብን ከሆነ ምክንያቱ የልብ አለመከፈት ነው፡፡ ቃሉን ሲሰማ ልቡ የተከፈተ ሰው ወዲያው ምን ላድርግ ብሎ ይጠይቃል ለንስሐም ቀጠሮ አይሰጥም ወደ ጥንት ኑሮውም አይመለስም፡፡

     መንፈሳዊ ሥራን ለመሥራት ወንጌልንም ለመስበክ ጽኑ መሻታችንን ዓይቶ ሁሉን የሚያመቻች ማሕየዊ(ሕይወትን የሚሰጥ) መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡በራዕይ ‹‹ሥራህን አውቃለሁ እነሆ በአንተ ፊት የተከፈተ በር ሰጥቼአለሁ ማንምም ሊዘጋው አይችልም›› በማለት በፍልድልፍያ ላለች ቤተክርስቲያን አለቃ ታላቃ የወንጌል ሥራ ከፊቱ እንዳኖረለት የነገረው የልብ መሻትን አይቶ ሁሉን የሚያመቻች እርሱ ስለሆነ ነው፡፡ ራዕ 3፥7-8

5. መስተፍሥሒ ማለት ደስ የሚያሰኝ ደስታን የሚመላ ማለት ነው፡፡ደስታ ከመንፈስ ፍሬዎች አንዱ ነው፡፡ይህ የመንፈስ ቅዱስ ደስታ በመብልና በመጠጥ በመሾምና በመሸለም እንደሚገኘው ዓይነት ጊዜያዊ ደስታ ወይም በኃጢአት የሚሆን ፍርድና ሀዘን የሚከተለው ደስታ አይደለም፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ደስታ ማለት እግዚአብሔርን በመፈለግና በመከተል፤በቅድስናው ሥፍራ ተገኝቶ በእምነት በእውነት ሆኖ በማምለክ በመድኀኒታችን የማዳን ሥራ፤ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ከእግዚአብሔር ጋር በሚኖረን ትርጉም ያለው ግንኙነት፤ ወንጌል ሲሰበክና ሰዎች ወደ ድኅነት ሲቀርቡ ወዘተ. . .እኒህንና እኒህን በመሳሰሉት ነው፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሥጢረ መንግስተ ሰማያት አዋቂዎች ነን በሚሉ ጻፎችና ፈሪሳዊያን ሳይታወቅ በመንፈሳቸው እንደሕጻናት የዋህ ለሆኑ ሐዋርያት ስለተገለጸላቸው. . . በመንፈስ ቅዱስ ሐሴት አደረገ ተብሎ ተጽፏል፡፡ ሉቃ 10፥21

     ሌላው መሐሪና ይቅር ባይ፤ ስመ ድኅነትና ስመ ሥርዓት ስለሆነው ስሙ መከራን ለመቀበል የተገቡ ሆነው ስለተገኙ ሐዋርያት ሐሴት ያደርጉ ነበር፤ደስታ ይሉሀል በሰማዕትነት ሥቃይ ውስጥ ሆነን ራሳችንን ለክርስቶስ አሳልፈን በመስጠታችንና ከእርሱ ጋር ለመሞት ስለተመረጥን የሚሰማን ደስታ ነው፡፡ በዚህ ዓለም በመንፈስ ቅዱስ ሀሴት ስለማድረግ ካሰብን ከዚህ የሚበልጥ ደስታ የለም፡፡ ለዚህ ሁሉ የሚያዘጋጅ የሚያበቃ በዓለም ከሚሆን ደስታም የሚለይ ስለሆነ ነው ጌታ መንፈስ ቅዱስ መስተፍሥሂ የተባለው፡፡ ማቴ 5፥11-12፤የሐዋ.ሥራ 5፥40-42

አንድም በዚህ ዓለም ያለን መከራ አልፈን በሃይማኖት ጸንተን በትሩፋት ሥራ ከብረን ከሥጋ ርስት ስንለይ በዘላለም ቤት የዚህን ዓለም መከራ እስክንረሳ በሚያደርስ ደስታ ያኖረናል መስተፈስሂ ይባላል፡፡ ራዕ 14፥13፤ሮሜ 8፥18

6. ከሣቲ፡-ሕይወትን የሚሰጥ ጌታ መንፈስ ቅዱስ በሕይወታቸው ደስ ለሚያሰኙት ወዳጆቹ ብዙ ነገር የተለያየ ምሥጢርን እንደየዐቅማቸው ይገልጥላቸዋል፡፡ ከቀድሞ ጀምሮ አካላዊ ቃል ዓለምን ለማዳን ከድንግል እንደሚወለድ ለነቢያት የገለጠ በእነርሱም አድሮ ለዓለም ያስተማረ እርሱ ነው፡፡ ‹‹ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ማሕየዊ ዘሠረፀ እም አብ ንስግድ ሎቱ ወንሰብሖ ምስለ አብ ወወልድ ዘነበበ በነቢያት…›› እንዲል ጸሎተ ሃይማኖት፡፡

     የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነትም መንፈስ ቅዱስ ያላደረበት አእምሮ ሊረዳው አይችልም፡፡ዓለም ይህንኑ(ነገረ ሥጋዌን) በተለያየ ፍልስፍናና አስተሳሰብ ለመተንተን እየሞከረ በስህተት ገደል የሚወድቅ ለዚህ ነው፡፡ስምዖን ጴጥሮስ በፊሊጶስ ቂሣርያ‹‹አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ›› ብሎ ሲመሰክር ጌታ መልሶ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጠልህም የሰማዩ አባቴ እንጂ(አሐቲ ሥምረት መሆኑን ልብ ይሏል) በማለት የነገረው፤ባጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጦ የታየ ጌታችንን አምላክ ወልደ አምላክ ብሎ ማመን ለሥጋዊአእምሮ ጠጣር በመሆኑ ነው፡፡

     ሐዋርያት ምሥጢረ መንግስትን እንዲያውቁ የሙሴና የነቢያት መጻሕፍትን ሁሉ እንዲያስተውሉና እንዲተረጉሙ በአጠቃላይ ሰማያዊ የሆነውን እውቀት ሁሉ የገለጠላቸው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ቅ.ጳውሎስ ‹‹…እንዲሁም ደግሞ ከእግዚአብሔር መንፈስ በቀር ለእግዚአብሔር ያለውን ማንም አያውቅም፡፡እኛ ግን ከእግዚአብሔር እንዲያው የተሰጠንን እናውቅ ዘንድ ከእግዘብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንም፡፡›› ብሏል ጨምሮም ‹‹ደግሞ የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታወቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ ስለ እኔ ለምኑ››በማለት ምስጢር ገላጭ የሆነ እርሱ ብቻ መሆኑን አሳውቋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ትንቢት መናገርም ሆነ ትንቢትን መተርጎም ከመንፈስ ቅዱስ መሆኑን ሲያስረዳ‹‹ይህን በመጀመሪያ እወቁ፤በመጽሐፍ ያለው ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም፤ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ፡፡ 2ጴጥ1÷20-21፤1ቆሮ2÷11-12፤ ኤፌ6÷19

ሰዎች በትዕቢት ሲያዙ ደግሞ የሚያነቡትን እንዳያስተውሉ ምሥጢርን ይሰውራል፡፡ ሐዋርያት ጌታችንን ለምን በምሳሌ እንደሚያስተምር ሲጠይቁት ‹‹ለእናንተ የመንግስተ ሰማያትን ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቷችኋል ለእነርሱ ግን አልተሰጣቸውም››ያለ ይህን ለማመልከት ነው፡፡ቅዱስ ጳውሎስም‹‹ወንጌላችን የተከደነ ቢሆን እንኳ የተከደነባቸው ለሚጠፉ ነው፡፡››ብሏል፡፡በቆሮንቶስ መልእክቱም ዓለም በጥበቧና በምርምሯ እግዚአብሔርን ለማወቅ እንዳልቻለች በተብራራ ሁኔታ ተገልጿል:: ማቴ13፥10-11፤ 1ቆሮ1÷18-27፤2ቆሮ4÷3 ስለዚህ ከትዕቢተኞች ምሥጢር የሚሰውር መንፈስ ቅዱስ ለትኁታን ደግሞ ስለሚገልጥ ከሣቲ ተብሏል፡፡

7. አለባዊ ማለት ማስተዋልን የሚሰጥ ማለት ነው፡፡ሰዎች ጌታ እግዚአብሔርን እንደ እግዚአብሔርነቱ መጠን ሳያከብሩት ሲቀሩና ኃጢአት መሥራት ሲደፋፈሩ ለማይረባ ከንቱ አእምሮ ተላልፈው ይሰጣሉ፡፡ከንቱ አእምሮ ማለት ማስተዋል የተሳነው ለመምረጥ ለመወሰን በሚሰራውም ነገር የሚጠብቀውን ውጤት(ፍርድ) ለመረዳት የተዘጋበት፤ ምክር የማይሰማና ተግሳጽ የማይቀበል ማለት ነው፡፡

     ማስተዋል የተነሳቸው ለከንቱ አእምሮ ተላልፈው የተሰጡ ሰዎች የጌታ እግዚአብሔርን መኖር ይክዳሉ በግብራቸውም ከእንስሳት አንሰው ይታያሉ፡፡‹‹ልብ እንደሌላቸው እንስሳት ሆኑ››ያለው መጽሐፉ እንደነዚህ ያሉትን ነው፡፡በነቢዩ በኢሳይያስ‹‹ሂድ ይህን ሕዝብ መስማትን ትሰማላችሁ አታስተውሉምም ማየትንም ታያላችሁ አትመለከቱምም በላቸው›› በሚል ጠባያቸው ተገልጿል፡፡ ኢሳ 6፥9፤ሮሜ 1፥20-28

     ጌታ መንፈስ ቅዱስ እውቀት በማጣት ጨለማ ላለ ሕዝብ እግዚአብሄርን የማወቅ ብርሃንን እንዲያይ ማስተዋልን ይሰጣል፡፡ዮሐንስ መጥምቅ ጌታችንን አያውቀው እንደነበርና ለእርሱም የገለጠለት መንፈስ ቅዱስ እንሆነ መስክሯል፡፡ዮሐ1÷3

ጌታችን ሐዋርያትን ብዙ ነገር ከነገራቸው በኋላ ከዚያም በላይ ሊነግራቸው ይችል እንደነበር እነርሱ ግን በነበሩበት ደረጃ ቢነግራቸው ለማስተዋል እንደማይችሉ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ግን እንደሚመራቸው (ማስተዋልን እንደሚሰጣቸው) እንዲህ ሲል ነግሯቸዋል፤‹‹የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም፡፡ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል…ዩሐ16÷12-13 ቤተክርስቲያን በቸርነቱ እየጠበቀ በምግብናው የሚመራት ጌታ መንፈስ ቅዱስን‹‹ሀበነ እግዚኦ አዕይንተ አእምሮ ወትረ ኪያከ ይርአያ ወአዕዛንነሂ ቃለ ዘባህቲትከ ይስምዓ››ስትል በጸሎቷ ትማልላለች፡፡ዓይነ ሥጋችን ግዙፉን ዓይነ ልቡናችን ረቂቁን፤አንድም ዓይነ ሥጋችን ሥነ ፍጥረትህን በማየት ዓይነ ልቡናችን ቸርነትህን ምህረትህን መግቦትህን በማስተዋል አንተን ብቻ ማየት(ማምለክ) እንድችል፤ዕዝነ ሥጋችንና ዕዝነ ልቦናችንምሕይወት የሆነ ያንተን ቃል ብቻ መስማት ይችል ዘንድ አቤቱ ስጠን ስትል ነው፡፡

     ካለ መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ጥበብን ይልቁንም መንፈሳዊ ጥበብን(ምሥጢርን) ገንዘብ አደርጋለሁ ማለት ከንቱ ነው፡፡የጠቢባንን ምክር የአዋቂዎችንም ማስተዋል የሚያስረሳቸው እርሱ በትኅትና በየዋህነት ደጅ ለሚጠኑ ሁሉ ግን ማስተዋልን ይሰጣል፤ፈቃዱ እንዱሁ ነውና፡፡


 

8. መስተናግር ማለት ሃይማኖትን፣ የጥበብን ቃል፣ ምሥጢርን የሚያናግር የሚያስተረጉም ማለት ነው፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ በበዓለ ሀምሳ በአይሁድ መካከል ቆሞ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ቢናገር በአንድ ጊዜ ስብከት ሦስት ሺ ሰዎች ማሳመን ችሏል፡፡ ይህ የሆነው ከቅዱስ ጴጥሮስ ዝግጅት ሳይሆን ‹‹ጉሽ የወይን ጠጅ ጠጥተዋል›› ብለው ሲያሙ ለነበሩ አይሁድ የተሰጠ የመንፈስ ቅዱስ መልስ ነበር፡፡ቅዱስ ጳውሎስ‹‹…ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን መግለጥ ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል፡፡ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፤ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል…ለአንዱም ትንቢትን መናገር…ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር…ይሰጠዋል››ሲል የመንፈስ ቅዱስን የማናገር ኃይል አብራርቷል፡፡እንግዲህ በዋናነት መንፈስ ቅዱስን መስተናግር(የሚያናግር)ስንል፡-

ሀ. ሀብተ ትንቢትን ሰጥቶ ኃላፍያትን መጻእያትን የሚያናግር

ለ.የጠፋውን ለመመለስ የጠመመውን ለማቅናት የጥበብን ቃል የሚሰጥ(የሚያናግር)

ሐ.የሃይማኖትን ቃል ለማቅናት እውቀትን(ምሥጢር በመተርጎም) የሚናገር

መ.ለእያንዳንዱ ነገድና ሕዝብ ቋንቋውን ተናጋሪ ኅብረተሰብን መስሎና ተካክሎ መናገር ማለት ነው፡፡ 1ኛ ቆሮ 12፥4-11

ከዚህ የሚልቀው ደግሞ እነሆ፡-

‹‹ለእርሱና ለአሕዛብም ምስክር እንዲሆን ስለ እኔ ወደ ገዥዎች ወደ ነገሥታትም ትወስዳላችሁ፤አሳልፈውም ሲሰጡአችሁ የምትናገሩት በዚያች ሰዓት ይሰጣችኋልና እንዴት ወይስ ምን እንድትናገሩ አትጨነቁ በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁም››ማቴ 10፥18-20

ጌታችን በሰማዕትነት ሰዓት ከነገሥታቱና ከጠቢባኑ በእኛ ያለውን እውነትና ተስፋ ለማስተሐቀር እንዲሁም በሀይማኖታችን ለመዘበት ለሚያነሱት ጥያቄና ክርክር እንዳንጨነቅ በዚያኑ ሰዓት በእኛ ውስጥ ያለ ጌታ መንፈስ ቅዱስ የምንናገረውንና ተከራካሪዎቻችንን የምናሳፍርበትን ቃል እንደሚሰጠን የተናገረው ማረጋገጫ ነው፡፡

9. መስተሥርዪ፡-መንፈስ ቅዱስ መስተሥርዪ ይባላል፡፡ኃጢአትን የሚያርቅ የሚያስወግድ የሚደመስስ ማለት ነው፡፡መንፈስ ቅዱ በአርባ በሰማንያ ከተጠመቅንበትና ከሥላሴ ልጅነትን ካገኘንበት ቀን ጀምሮ በእኛ ያድራል፡፡ሃይማኖትን ካልካድን በስተቀር አይለየንም፡፡ይህን ሲያይ ነው ቅዱስጳውሎስ ‹‹የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖርባችሁ አታውቁምን?›› ያለው፡፡ 1ኛ ቆሮ 3፥16

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአታችንን ሊሽር በደላችንንም ሊደመስስ የመጣ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ አሐቲ ሥምረት ነው፡፡ኤፍሬም ሶርያዊ‹‹እስመ በፈቃዱ ወለሥምረተ አቡሁ ወመንፈስ ቅዱስ መጽአ ወአድኃነነ›› እንዳለ፡፡ ውዳሴ ማርያም ዘሠሉስ፡፡ በአባቱ በራሱና በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ መጥቶ አዳነን ማለት ነው፡፡ይህቺ ሥምረት(ፈቃድ) አንዱ ቀድሞ አስቦ ለሌላው የሚገልጻት መቀዳደም መለያየት ያለባት አይደለችም አንዲት ናት አንጂ፡፡ሰው በልቡ የሚያስበው ከመንፈሱና ከቃሉ መወቀዳደም እንደሌለበት ማለት ነው፡፡በመሆኑም በሰው ልጅ መዳን ውስጥ የፈቃድ መለያየት የለምና መንፈስ ቅዱስመስተስርዪ ይባላል፡፡አንድም

     በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸሙ ምሥጢራት ሁሉ የሚፈፀሙ(የሚከብሩ)በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡በጥምቀት ለሚገኝ ሥርየተ ኃጢአት ፈጸሚው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ኃጢአተኛ ንስሐ በሚገባ ወቅት በካህኑ ላይ አድሮ የሚናዝዝ የኃጢአትንም ሥርየት የሚሰጥ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ጌታችን ከትንሳኤው በኋላ ‹‹እፍ ብሎ መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፤ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል›› በማለት ለሐዋርያትሥልጣነ ክህነትን ሰጥቷቿል፡፡ በዚህ ዓለም የካህናት ተግባር ሰዎች ሁሉ ስለኃጢአታቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቅርታንና ሥርየትን እንዲያገኙ ማገልገል ነው፡፡በጥምቀት፣በማስተማር፣በመምከርና በመገሰፅ፣በመናዘዝ፣እንዲሁም ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በማቀበል በስሙ የሆነ የኃጢአት ሥርየትን መስበክ የምሥጢረ ክህነት ዋና ተግባር ነው፡፡በመሆኑም ክህነትን ከመስጠት ጀምሮ ምሥጢራት ሁሉ የሚፈጸሙ በመንፈስ ቅዱስ በመሆኑ መስተሥርዪ ተብሏል፡፡ ዮሐ 20፥22-23

     መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ ቅዱስ በሚመጣ ጊዜ ስለ ሶስት ነገር ዓለምን እንደሚወቅስ ተናግሯል፡፡ ‹‹…እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፡፡ ስለ ኃጢአት በእኔ ስለማያምኑ፤ ስለ ጽድቅም ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤ ስለ ፍርድም የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው›› ዮሐ16÷8-11

     በዘመነ ሐዲስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ተገልጦ ዓለምን ማዳኑን ከመካድ በላይ ኃጢአት የለም፡፡መንገድ ሕይወትና እውነት የተባለች በእርሱ ያለን ይህቺ ሃይማኖት ናት፡፡ሃይማኖትን መካድ ከመንፈስ ቅድስ ልጅነት የመለየት መጨረሻው ምልክት ነው፡፡

     በአንጻሩ ወረደ፣ተወለደ፣ተሰቀለ፣ሞተ፣ ተነሣ፣ ወደ ሰማይ ወደ አባቱ ዐረገ፣ ፣ዳግመኛም ለፍርድ ይመጣል ብሎ ከመመስከር የበለጠ ጽድቅም የለም፡፡ ቅ.ጳውሎስ‹‹እግዚአብሔርን የመምሰል ምሥጢር ያለ ጥርጥር ታላቅ ነው፤በሥጋ የተገለጠ፣ በመንፈስ የጸደቀ፣ለመላእክት የታየ፣በአሕዛብ የተሰበከ፣ በዓለም የታመነ፣በክብር ያረገ››1ጢሞ3÷16 ብሎ ክርስተናን በጥቅል ያስቀመጠ ለዚህ ነው፡፡ሐዋርያት በአጽናፈ ዓለም ጻድቃን በገዳም ሰማዕታት በደም የፈጸሙት ጽድቅም ይኸው ነው፡፡ ሁሉም አምላክ ሰው ሰውም አምላክ የመሆኑ ሕያው የሕይወት ምስክሮች ናቸው፡፡

     መንፈስ ቅዱስ የዚህ ዓለም ገዢ የተባለ ዲያቢሎስ እንደተፈረደበትም አብስሯል፡፡ፍርዱ ግን በዲያብሎስ ብቻ አይደለም በክህደት በኃጢአት እርሱን በሚመስሉት ላይ ሁሉ እንጂ፡፡ዮሐንስ በወንጌሉ‹‹በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና፡፡…በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤በማያምን ግን በአንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈረዶበታል››ዮሐ3÷16-19 ብሎ የዲያብሎስን የክህደት መንገድ የመረጡ ከጸጋ መንፈስ ቅዱስ ከመንግስተ እግዚአብሔር በአፍአ የሚጣሉ መሆናቸውን ገልጿል፡፡ ዲያብሎስን በግብር በክህደት የሚመስሉት ሁሉ ፍጻሜያቸው እርሱ በሚኖርበት መኖር በእርሱ ላይ የተፈረደውንም መቀበል ነው፡፡

     ጌታ መንፈስ ቅዱስ ይህን ሁሉ የሚሠራ እኛ ለዘላለም በሕይወት እንኖር ዘንድ ነው፡፡ ራሳችንን ለፈቃዱ ካስገዛን፤የእርሱ ማደሪያ መቅደሶች መሆናችንን አውቀን ህዋሳቶቻችንን ሁሉ በቅድስና ከጠበቅን በቅዱሳን ላይ አድሮ የሥራውን ሥራ በእኛም አድሮ ይሠራል፡፡ ሕይወትን ከሚሠጥ ከእርሱ ጋርም ለዘላለም በሕይወት እንኖራለን፡፡ሃይማኖትን ከመልካም ሥራ አስተባብረን እንድንይዝ በጌታችን በደሙ መገዛታችንንም ከንቱ እንዳናደርግ በማስተዋልም እንድንኖር ነው ቅዱስ ጳውሎስ‹‹ለቤዛም ቀን የታተማችሁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ››ያለን፡፡ኤፌ3÷30 የእግዚአብሔር ልጆች የመንግሥተ ሰማያት ዜጎች የመሆናችን ማረጋገጫ ማኅተማችን እርሱ ነውና፡፡

ዓለማትን የፈጠረ በነቢያት አድሮ የተናገረ በሐዋርያትም እውነትን ያስተማረ ጻድቃን ሰማእታትን ለገድል ያዘጋጀ እግዚአብሔርን መንፈስ ቅዱስ ሕይወታችንን ተረክቦ ይመራልን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁን! ጌታ ቢፈቅድ ብንኖር በሌላ የሕይወት ቃል እስክንገናኝ የአብ ቸርነት የወልድ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ ሕብረት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን!

ግንቦት2007

 

ቀሲስ ታምራት ውቤ

Read more...

ታሪከ አበው: ኖህ ክፍል 2

Download
Name
Play
Size
Duration
download
ኖህ ክፍል 2
yeneta

45.4 MB
1:08:42 min

Read more...

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል አምስት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን የሚያውቅ የባህርይ አምላክ ስለመሆኑ፤

መግቢያ፡- ባለፉት ሳምንታት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ "ሁሉን ቻይ" አምላክ መሆኑን በተረዳ ነገር አይተናል፡፡ በዛሬው ጹሑፋችን አምላካዊ ባህርያት ከሆኑት አንዱን "ሁሉን ማወቅ" ከመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ በማስደገፍ እናያለን፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ምስጢሩን ይግለጽልን!

ሁሉን ማወቅ የእግዚአብሔር የብቻው /የተለየ/ ባህርዩ ነው፡፡ በሰማይም ሆነ በምድር ወይም በውቅያኖስ፣በብርሃንም ሆነ በጨለማ ፣ በቁሳዊውም ሆነ በመንፈሳዊው ዓለም እርሱ የማያውቀው ከእርሱ ተሰውሮ የሚፈጸም አንዳች ስንኳ የለም፡፡ ሁሉንም ከመሆኑ በፊት እንደተደረገ አድርጎ ያውቀዋል፡፡ በጸሎተ ኪዳን እንተፃፈ " እምቅድመ ህሊና ኲሎ የአምር፣ ወእምቅድመ ህሊና ይፈትን" ከህሊና አስቀድሞ ያውቃል፣ ከሀሳብም ቀድሞ ይመረምራል፡፡ ዓለምን ጅማሬው ላይ ሆኖ ፍፃሜውን ያውቀዋል፡፡ በአጭር ቃል ከእርሱ ምንም ምን አይሠወርም የክፍዎችንም ሆነ የበጎዎችን ምክር ያውቃል፣ የጠቢባንንም አሳባቸውን ይመረምራል፡፡ ከመሆኑ አስቀድሞ እንጂ ከተደረገ በኋላ ተመራምሮ በነገሩ የሚደርስ አይደለም፡፡ በመሆኑም አኛንም ማንም ከሚያውቀን ይልቅ ከራሳችንም በላይ ያውቀናል በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ተብሏል፡፡

1ሳሙ 2፥3 " አትታበዩ በኩራትም አትናገሩ፡ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና…"

1ኛ ዮሐ 3፥20 " እግዚአብሔር ከልባችን ይልቅ ታላቅ ነውና ሁሉንም ያውቃል"

ይህ እንዲህ ከሆነ "ሁሉን አዋቂነት" የሚለው ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀፀል ይችላል ወይ? የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምላሽ "በትክክል" የሚል ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ እነሆ፡፡

ማቴ9፥1-8 ጌታ እየሱስ ክርስቶስ በአልጋ የተኛ ሽባ ወደ እርሱ ባመጡ ጊዜ ሽባውን"አንተ ልጅ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ" አለው፡፡ ከጻፎች ግን አንዳንዶቹ በልባቸው ይህስ ይሳደባል አሉ፡፡ ኢየሱስም አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አለ ስለምን በልባችሁ ክፉ ታስባላችሁ?...

ማቴ 12፥15 ጌታችን በሰንበት ስለፈወሰ ፈሪሳውያን ሊገድሉት ሲማከሩ ምክራቸውን አውቆ ከዚያ ፈቀቅ አለ ይላል፡፡

ማቴ 12፥22-27 ሕዝቡ በአጋንንት ላይ ባለው ሥልጣን ሲደነቁ ፈሪሳውያን ግን በአጋንንት አለቃ በብዔል ዜቡል አጋንንትን ያወጣል በማለት ሲያስቡ ኢየሱስ ግን አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው እርስ በርሷ የምትለያይ መንግስት አትፀናም…

ማቴ 17፥24-27 ቀረጥ ሰብሳቢዎች ጰጥሮስን በውጭ አግኝተው መምህራችሁ ግብር አይገብርምን? ብለው ሰለጠየቁት ጴጥሮስ ይህን ሊናገር ወደ ቤት ሲገባ አስቀድሞ የሆነውን አውቆ ዓሣ አጥምዶ ያገኘውን እንዲከፍል ነግሮታል፡፡

ሉቃ 5፥1-11 ቅዱስ ጴጥሮስ ሌሊቱን ደክሞ ያልሆነለትን በጌታችን ትዕዛዝ ብዙ ዓሣ በመያዙ ቢደሰትም በታላቅ ፍርሃት ጌታን "እኔ ኃጥአተኛ ሰው ነኝና ከእኔ ተለይ" ብሎታል፡፡ መተርጉማን ይህን የቅዱስ ጴጥሮስን ቃል ሲፈቱት የባህሩን ውስጥ እንዲህ ያወቀው የእኔንማ ልብ እንዴት ይመረምረው ብሎ እንደፈራ ያትታሉ፡፡

ሉቃ 7፥36-50 መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በስምዖን ፈሪሳዊ ቤት ለምሳ በተቀመጠበት ወቅት ባለ ሽቶዋ ማርያም እግሩን እየሳመች በእንባዋ እያጠበችና በፀጉርዋ እያበሰች ሽቶ ቀብታ ሰለኃጢአቷ ሥርየት በአርምሞ ስትማፀ ስምዖን ፈሪሳዊ አይቶ ይህስ ነብይ ቢሆን ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደሆነች እንዴትስ እንደነበረች ባወቀ ነበር ኃጥአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ፡፡ለዚህ ሰው የልቡን አውቆ  ምን ዓይነት አስደናቂ መልስ እንደሰጠው ቃሉን አንብብ፡፡

ሉቃ 8፥43-48 12 ዓመት ደም ይፈሳት የነበረች ሴት የነበረች ሴት ጌታን ህዝቡ እያገፋው ሳለ ተሰውራ የቀሚሱን ዘርፍ በመንካቷ ተፈወሰች ጌታም ማን ነው የነካኝ ብሎ ሲጠይቅ ሐዋርያት ህዝቡ ይገፉሃል ማነው የነካኝ ትላለህን? ሲሉት አንድ ሰው ዳሶኛል ኃይል ከእኔ እንደወጣ እኔ አውቃለሁና ብሎ ነው የመለሰው ሴቲቱም እንዳልተሠወረች ባየች ጊዜ እየተንቀጠቀጠች መጥታ በፊቱ ተደፋች የተደረገላትንም በህዝቡ ሁሉ ፊት መሠከረች፡፡

ሉቃ 22፥31-34 ጌታችን እንደሚያዝና ሁሉም ጥለውት እንደሚሸሹ በተናገረበት ምሴተ ሐሙስ ቅዱስ ጴጥሮስ ሌሎች ቢክዱህ እኔ አልክድህም ብሎ ለሠጠው የትምክህት መልስ" ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ እንደሚክደው ቀድሞ ነግሮታል፣ ይኸውም እንደቃሉ ተፈፅሟል፡፡

ዮሐ2፥5 " ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፡፡ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና፡፡

ዮሐ 1፥47-50 ፊልጶስ ናትናኤልን ጋብዞ ወደ ጌታችን ባመጣው ሰዓት ጌታ "በልቡ ተንኮል የሌለበት የእስራኤል ስው እነሆ" በማለቱ ናትናኤል ከወዴት ታውቀኛለህ? ቢለው ፊልጶስ ሳይጠራህ ከበለስ በታች አየሁህ የሚል መልስ ሲሰጠው" መምህር ሆይ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ" በማለት እርሱ ሁሉን አዋቂ አምላክ ወልደ አምላክ መሆኑን መስክሯል፡፡

ዮሐ4፥1-መጨረሻ  በተፃፈው ፍፁም የሚመስጥ ታሪክ ሳምራዊቷ ሴት ለሀገሯ ሰዎች ከጌታችን ጋር ስለነበራት ቆይታ ስትገልፅላቸው ወደ እርሱ እንዲመጡም ስትጋብዛቸው "ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ…" ብላለች ቁጥር 29

ዮሐ6፥15 እንጀራ በልተው ሲጠግቡ እርስ በርሳቸው ከሆነስ አይቀር ስንራብ እያበላ ፣ስንጠማ እያጠጣ፣ስንታመም እየፈወሰ፣ስንሞት እያሰናዳ ቢገዛን መልካም በሆነ ኑ እናንግሠው ብለው ያሰቡትን አውቆ ከአጠገባቸው ፈቀቅ ብሎ ወደ ተራታ ወጣ ይላል፡፡

ዮሐ11፥1-መጨረሻ ፡- በቦታው በአካል ባይገኝም ስለአልዓዛር መታመምና መሞት ቀድሞ ለሐዋርያት ነግሯቸዋል፡፡

v  ጌታችን ስለሞቱና ትንሣኤው አስቀድሞ ተናግሯል፡፡

ማቴ 24፥1-መጨረሻ፡- የዓለም መጨረሻና የዳግም ምፅዓቱ ምልክቶችን አስቀድሞ ተናግሯል፡፡        ዮሐ16፥29-30 ሐዋርያት"እነሆ አሁን በግልጥ ትናገራለህ፣በምሳሌም ምንም አትናገርም ሁሉን እንድታውቅ ማንምም ሊጠይቅህ እንዳትፈልግ አሁን እናውቃለን፡፡

ዮሐ21፥15-17 በጥብርያዶስ ባህር ዳርቻ ጌታችን ከስምዖን ጴጥሮስ ጋር በነበረው ቆይታ "ትወደኛለህን?" ብሎ ሦስት ጊዜ ለጠየቀው ጥያቄ የሰጠው የመጨረሻ ምላሽ "ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ታውቃለህ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ " የሚል ነው፡ በዚህም ሁሉን አዋቂ መሆኑን አስረግጦ መስክሯል፡፡ በመቀጠል ጌታችንም ቅዱስ ጴጥሮስ በኔሮን ቄሣር ዘመን በምን ዓይነት ሞት እግዚአብሔር ያከብር ዘንድ እንዳለው ነግሮታል ይህም ሁሉን አወቂ መሆኑን ያስረገጠበት መንገድ ነው፡፡

ራስን መመዘኛ /መመርመርያ/ ጥያቄ!

 

.የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አዋቂነቱ በእኔ ሕይወት ውስጥ ያለው ተፅዕኖ ምን ያህል ነው?

ለ. በእርግጥ እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ መሆኑን በእውነት አምናለሁ?

. እግዚአብሔር ከሁሉን አዋቂነቱ ወሰን ተሠውሬ ኃጢአት ሠርቼ አውቃለሁን?

መ. ቅዱስ እግዚአብሔር / ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ / ከልቤ ጋር ያለው ግንኙነት ምን ያህል ነው? እንዴትስ እረዳዋለሁ?

 

v  በሀገር ውስጥ ላላችሁ ለጥያቄዎቹ መልስና ሀሳባችሁን በሪፖርት(በወረቀት) በጉባኤ ቀን ትሰጣላችሁ፡፡

ይቆየን!

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Read more...

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል ዓራት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

       በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

መግቢያ

        የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ቻይነቱ በሞት ላይ በነበረው ሥልጣንም ገልጿል፡፡ ሞት የኃጢአት ውጤት(ደመወዝ) ነው፡፡ ለሞት ያልተገዛ ፍጥረትም የለም፡፡ ከአዳም ጀምሮ የአዳማዊው ተፈጥሮ ተጋሪ የሆኑ ልጆቹና ለአዳም የተፈጠሩት ፍጥረቶች ሁሉ በሞት ጥላ ሥር ወድቀዋል፡፡ ርዕሳነ አበው፣ነብያት፣ነገሥታት፣ካህናት፣ሁሉ በሞት መዳፍ ተያዙ ማምለጥም የታቻለው ወይም ይህን የሞት ፍርድ ሊያስቀር የቻለ አንድ ስንኳ አልተገኘም፡፡

ይህንኑ ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ ምዕ 5፥12-21 በጥሩ ሁኔታ አብራርቶታል፡፡ "…ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት… ነገር ግነ በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ኃጢአትን ባልሠሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ…" ጨምሮም "…የኋላኛው ጠላት የሚሻረው ሞት ነው፤ ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዝቶአልና፡፡ነገር ግን ሁሉ ተገዝቶአል ሲል ሁሉን ካስገዛለት በቀር መሆኑ ግልጥ ነው" ፡፡ 1 ቆሮ 15፥25-28 በማለት የሞትን ሥልጣንና የሞትን ሥልጣን ሰብሮ ኃያልነቱን(ሁሉን ቻይነቱን) የገለፀውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥራ ግልፅ አድርጓል፡፡

      አበው ለብዙ ዘመናት ከዚህ የሞት ባርነት ነፃ ሊያወጣቸው ወደሚችል በብዙ ልመና ሲቃትቱ ኖረዋል፡፡ ጊዜው ሲደርስ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ ሞትን ሻረው፡፡ ሞት ነግሦባት በነበረች ምድር ለመጀመርያ ጊዜ " እሰቀላለሁ፣ እሞታለሁ በሦስተኛውም ቀን እነሳለሁ" እንዲሁም " ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል እኔ በፍቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወስዳትም፡፡ ላኖራት ሥልጣን አለኝ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ፤ይህቺን ትዕዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ፡፡" በማለት ሞትን ያስደነገጠ የአዳምን ተስፋ ያረጋገጠ አዋጅ ተሰማ፡፡ ዮሐ 10፥18፣ ማቴ 16፥21

     መግደልና ማዳን የእግዚአብሔር ብቻ ሥልጣን መሆኑ በቅዱሳት መጻሕፍት የተረጋገጠ ነው፡፡ ኦሪ.ዘዳ 32፥39፣ 1ሳሙ 2፥6፣ ማቴ 10፥28-31 ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን "ነፍሴን ላኖራትም ላነሣትም ሥልጣን አለኝ" በማለት በሞት ላይ ያለውን ገዢነቱን በተጨማሪም የመግደልና የማዳን መለኮታዊ ሥልጣን ያለው ወይም እርሱ እራሱ እግዚአብሔር መሆኑን ገለፀ፡፡ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች ሰዓትም የተናገረውን አስተውል፡፡ "ኢየሱስም በታላቅ ድምጽ ጮኾ አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ አለ፡፡" ይህ ጩኸት ይህ ቃል የሞትን ሥልጣን ያረጋገጠ የዲያቢሎስ መንግስት የቆረጠ ነው፡፡ ሉቃ 23 ፥46

ልዩ ከምትሆን ቅድስት ትንሣኤው በፊትም በኢየሩሳሌም አውራጃዎች እየተዘዋወረ ሲያስተምር ሙታንን በማስነሳት እርሱ በሞት ላይ ፍፁም ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑን አሳይቶናል፡፡

-    ሉቃ 8፥49-56 ፡- ኢያኢሮስ የተባለው የምኩራብ አለቃ ልጁ በሞተችበት ወቅት ጌታችን በቃሉ አስነስቷታል፡፡ "አንቺ ብላቴና ተነሺ" ብቻ በማለት

 

-    ዮሐ 11፥1-44 ፡- የጌታ ወዳጅ አልዓዛር ሞቶ በተቀበረ በአራተኛው ቀን ጌታችን ትንሣኤና ሕይወት እርሱ መሆኑንና በእርሱ የሚያምን ቢሞትም እንኳ ህያው እንደሚሆን ካወጀ በኋላ ወደመቃብር ሔዶ "አልዓዛር ሆይ ወደ ውጭ ና" በማለት አስነስቶታል፡፡

በዚህ ላይ ምናልባት አንዳንዶች ነቢያት፣ሐዋርያት ድውይ ፈውሰዋል፣ምውት አንስተዋል ይህን አደረጉ ብለን "ሁሉን ቻይ" እንደማንላቸው ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስንም እንዲሁ ነው ብለው ሊከራከሩ ይችላሉ፡፡ 1ኛነገ 17፥17-24፣ 2ኛ ነገ 4፥32-37፣ ሐዋ.ሥራ 9፥40

መልስ

1ኛ- ነቢያትም ሆኑ ሐዋርያት ሙት እስከማንሳት የደረሱት ከልዑል እግዚአብሔር በተሠጣቸው ሥልጣን ጾመው፣ ጸልየው፣ ወድቀው፣ ተነስተው ነው፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ጥቅሶች የሚያመለክቱትም ይህንኑ ነው፡፡ ማር16፥17፣ ሉቃ 10፥17-20፣ዮሐ 14፥12-14፡ እውነት እውነት እላችኋለው በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፣ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል… ማናቸውም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ፡፡ ያለውን ቃልኪዳን ይጠብቅላቸዋል፡፡ የእርሱ ግን መጾም፣መጸለይ፣ መውደቅ፣መነሣት ሳያስፈልገው በሥልጣኑ ነው፡፡

2ኛ- ከነቢያትም ሆነ ከሐዋርያት ሙት እስከማንሳት የደረሱ ሁሉ በመጨረሻ እነርሱ ራሣቸው በሥጋ ሞት ተይዘዋል፡፡ ጌታችን በትንሣኤ ዘጉባኤ እስኪያስነሳቸውም ይጠብቃሉ፡፡ሙት ያስነሱ እነርሱ ለራሳቸው ግን አስነሺ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እርሱም ትንሣኤ ሕይወት የተባለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለእርሱ ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ይህንኑም ለማስረዳት ነው ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት ሰዓት እንኳ ብዙ ሙታን ተነስተው በኢየሩሳሌም የታዩት፡፡ በማቴ 27፥51-54 መላእክትም ለሴቶቹ " ሕያዋን ከሙታን መካከል ስለምን ትሹታላችሁ እርሱ በዚህ የለም ተነሥቶአል" ያሉአቸው፡፡ ሉቃ 24፥6

         በእነዚህ ከብዙ በጥቂቱ አእምሮን ለማንቃትና እምነትን ለማፅናት ከተጠቀሱት በተጨማሪ ብዙ የመፅሐፍት ቅዱስ ክፍሎችና የአበው ትምህርት ሁሉን ቻይነቱን አምልተው አስፍተው ገልፀውታል፡፡ ያን በማንበብና በማስተዋል የበለጠ መጠቀም ያስፈልጋል፡፡ በሚቀጥለው አምላካዊ ባህርያት ከሆኑት "ሁሉን አዋቂ" ስለመሆኑ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም እንማራለን፡፡

ይቆየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ጥቅምት 2005

Read more...

ታሪከ አበው: ሄኖክ እና ኖህ ክፍል 1

Download
Name
Play
Size
Duration
download
HenokAndNoahpart1

50.5 MB
55:12 min

Read more...

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ: ክፍል ሦስት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

         በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!

            በቀደመ ጽሑፋችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ቻይ አምላክ መሆኑን ድንቅ በሆነ ጽንሰቱ፣ ልደቱና በልጅነት ወራት አስደናቂ ህይወቱ ተመልክተናል፡፡ በይቀጥላል ጌታችን በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠምቆ ራሱን በትምርቱና በተዐምራቱ በገለጠበት ወቅት የህንኑ አስረግጧል፡፡

ዮሐ 2፥1-12 ፡- በተገለጠው ተዐምራት ጌታችን ውሃውን ወደ ወይን መቀየሩን እናውቃለን፡፡ የውሃ እና የወይን ባህርይ በውስጣቸውም የሚይዙት ውሁድ(Substance) የተለያየ እንደሆነ የተረዳ ነገር ነው፡፡ ጌታ በዚህ ተዐምራቱ ካልነበረ(ከሌለ) ነገር አንድን ነገር ማምጣት(መፍጠር) የሚችል መሆኑን አሳይቶናል፡፡

ዮሐ 5፥1 ፡- 38ዓመት ልምሾ ሆኖ እንደትኋን ካልጋ ተጣብቆ የኖረውን መፃጉዕ በቃሉ ብቻ    መፈወሱ ሁሉን ቻይነቱን ያስረዳል፡፡

ዮሐ 9፥1 ፡- በደረቅ ግንባር ላይ ዓይን መፍጠሩም እንደዚያው በዚሁ ምንባብ ላይ ዓይኑ  የበራለት ሰው በሰጠው ምስክርነት "…ዓለም ከተፈጠረ የዕውርን ዓይን የከፈተ ከቶ አልተሰማም" ማለቱ የጌታችንን ሁሉን ቻይነት የሚያስገነዝብ ምስክርነት ነው፡፡

ማቴ 9፥27-31 ፡- ባለው ተመሳሳይ ታሪክም ሁለቱ ማየት የተሳናቸው ሰዎች እነዲምራቸው  ሲለምኑት "ይህን ማድረግ እንድችል ታምናለችሁ?" ብሎ ነበር የጠየቃቸው ሁሉን ማድረግ ከሚችል ከእርሱ በቀር በሥልጣን ይህን መናገር የሚችል ይኖራልን?

ሉቃ 13፥10-17 ፡- 18 ዓመት በድካም መንፈስ ጎብጣ የኖረች ሴት ሌሎችም በዚህ ጹሑፍ ያልተጠቀሱ ተዐምራቶች የሁሉን ቻይነቱ ማስረጃዎች ናቸው ወንጌል ይህን በአንድ ቃል ሲያጠቀልለው "ህሙማንን ሁሉ ወደ እርሱ አመጡለት እርሱም ፈወሳቸው" ይላል ከመጣው ውስጥ ተስኖት ሳይፈውሰው የመለሰው አንድ ስንኳ የለም፡፡

በተፈጥሮ ላይ ሁሉን ቻይነቱን ሲገልፅ

ሉቃ 5፥1-10 ፡- ስምዖን ጴጥሮስና ጓደኞቹ ዓሣ ማጥመድ ሌሊቱን ሙሉ ሞክረው ተስኗቸው   ቀርተዋል፡፡ ጌታ ወደ ታንኳይቱ ገብቶ መረባቸውን በታንኳይቱ በስተቀኝ እንዲጥሉ ሲያዝ ሌሊቱን ደክመው መያዝ እንዳልቻሉ እንደቃሉ ግን መረቡን እንደሚጥሉ ገልፀው ቢጥሉ መረባቸው እስኪቀደድ ዓሣ ማጥመድ ችለዋል ይህም በተፈጥሮ ላይ ያለውን ኃይል ያሳያል፡፡

ማቴ 8፥22-25 ፡- ሐዋርያት የሚቀዝፉትና ጌታ ከበስተኋላ ያንቀላፋባት ታንኳ በብርቱ ማዕበል ስትንገላታ ባህሩም ሊደፍናት ሲቀርብ ሐዋርያት ጌታን ቀስቅሰው "ስንጠፋ አይገድህምን?" ባሉት ጊዜ ጌታ የእምነታቸውን ማነስ ወቅሶ ነፋሱን እና ማዕበሉን ገሠፀ ታላቅ ጸጥታም ሆነ ሐዋርያትም ሁሉን ቻይነቱን በተረዱ ወቅት "ነፋሳትና ባህር ስንኳ የሚታዘዙለት እርሱ ማንው? ብለው ሰገዱለት ይህም በተፈጥሮ ላይ ያለውን አዛዥነት በግልፅ ያስረዳል፡፡

ማቴ 14 ፡-በዚህ ሁለት ታላላቅ ተዐምራት ተደርገዋል፡፡ የመጀመርያው በአምስት ቂጣና በሁለት ዓሣ አምስት ሺህ ያህል ወንዶች ሴቶችን ህፃናት ሳይቆጠሩ መግቦ 12 ቅርጫት ፍርፋሪ ማስነሳቱ ሲሆን ሁለተኛው ሐዋርያት በባህሩ መካከል ሳሉ ባህሩን እነደየብስ እየረገጠ መምጣቱ፤ ጴጥሮስ ተጠራጥሮ ሊሰጥም ሲል በውሃ ላይ ቆሞ ውሃ ውስጥ የሚሰጥምን ማውጣቱ ለሁሉን ቻይነቱ መጋለጫ አይደለምን?

          እኒህ ከላይ የተገለፁት ተዐምራት ሁሉ ከአእምሮ በላይ የሆኑ ቢሆኑም ለሰው ልጅ በተሰጠው ደካማ ቋንቋ ስለተፃፉ ግን ውጣቸውን በመንፈስ ለመመርመርና ለማድነቅ ካልተዘጋጀን የሚፈጥሩብን ስሜትም እንዲሁ ደካማ ነው፡፡ በእምነት ለማደግ በቅዱስ እግዚአብሔር ፀጋ ለመበልፀግ ለሚጋደሉ ግን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ዓለማትን የፈጠረና ሁሉ በእርሱ ትዕዛዝ የሚመራ መሆኑን ለመረዳት ታሪኮቹ ከበቂ በላይ የሆኑ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ባነበብነው መልዕክት ጌታ መንፈስ ቅዱስ ህሊናችንን ለእውነታ ምርኮ ልቦናችንን  ለፍፁም አምልኮ የተዘጋጀ እንዲሆን ይርዳን!

ይቆየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቀሲስ ታምራት ውቤ

 

ጥቅምት 2005

Read more...
Subscribe to this RSS feed

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ