ዐቢይ ፆም
Featured
፪. ቅድስት፡- በዚህ ዕለት የሚነበቡት ምንባባት የቅድስና ህይወት በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ ስለመሆኑና እኛም እንዴት መኖር እንዳለብን የምንመካከርበት ነው፡፡
ምስባክ፡- እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ
አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ
ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ፤የሚል ነው፡፡ መዝ ፺፭፡፭
ሲተረጎም፡- እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ
ሃይማኖትና ምግባር በፊቱ ነው
ቅድስናና ታላቅ ምስጋናም በመቅደሱ ውስጥ ማለት ነው፡፡
-እውነት ነው ከእርሱ በቀር ሰማያትን የሠራ በክብርም ያስጌጣቸው የለም፡፡ የተሠሩትም ለጥቅማችን ነው፡፡ ለፍጡራን መኖሪያና(እርሱ ባወቀ) ለብርሃናት መመላለሻ ከመሆንም ባለፈ የቃሉን ብርታት የክብሩን ገናንነት የሚመሰክሩ ኃይላት ናቸው፡፡“ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ“ እንዲል ዳዊት፡፡ የልዑል እግዚአብሔርን ታላቅነት በጥቂቱ እንኳ ለመረዳት ብትሻ በሌሊት በጠፈር ሰምይ እንደስንዴ የተዘሩትን ከዋክብት ተመልከት፡፡ መዝ 18፥1
በህዋሳይንስ known Universe(የታወቀ ዓለም(ህዋ)) እና Unknown Universe(ያልተደረሰበት ዓለም(ህዋ)) የሚባል አለ፡፡ በታወቀው ዓለም(ህዋ) ከመቶ ቢልዩን በላይ የሆኑ ጋላክሲዎች እንዳሉ ይታመናል፡፡ ከእንዚያ አንዱ የእኛይቱ ያለችበት ጋላክሲ ሚልክዌይ ተብሎ ይጠራል፡፡ በእኛ ጋላክሲ ብቻ ከ300-500 ቢሊዮን የሚደርሱ ከዋክብት እንዳሉ ይታመናል፡፡ ከመቶ ቢልዮን በላይ ባሉ ጋለክሲዎች ስንት ከዋክብት ሊኖር እንደሚችል ገምት ለዚያውም በታወቀው(በተደረሰበት) ህዋ (Known Universe)፡፡ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል ትችሉ እንደሆነ የሰማይ ከዋክብትን ቁጠሩ፤እርሱ ግን ሁሉንም በየስማቸው ይጠራቸዋል፤በኃይሉ ብዛትና በችሎቱ ብርታት አንድ ስንኳ አይታጣውም፡፡ኢዩብ 38-39፣ ኢሳ 40፥18-26፤መዝ
ልብ በል እኒህ ሁሉ ሰማያትን፣ለማሰብ እንኳ የሚከብዱን ግዙፍ ዓለማት በልዑሉ ዘንድ ግን እፍኝ እንኳ አይሞሉም፡፡ ለዚህ ነው ኤሊሁም“ እነሆ እግዚአብሔር ታላቅ ነው፤እኛም አናውቀውም“ ቅዱስ አጲፋንስዩስም “ከሰማነው በላይ ግሩም ነህ፤ከተነገረንም በላይ ድንቅ ነህ“ በማለት በአንክሮ የቃተቱት፡፡ ኢዩብ 36፥26 ቅዳሴ ኤጲፋንዩስ
-ገናንነቱን እንዲህ ነው ብለን ልንናገረው የማንችለው አምላክ ሃይማኖት ምግባር በፊቱ ነው ይህ ማለት የሰው ሁሉ ሃይማኖትና ምግባር በፊቱ የተገለጠ ነው፡፡ የሚሠወረው የለም ሲል ነው፡፡ አንድም ሃይማኖትን ከምግባር አስተባብረው በቅድስና በምስጋና በመቅደሱ ፀንተው የሚኖሩ በፊቱ በክብር ናቸው ሲል ነው፡፡ አንድም በሃይማኖት በምግባር የጸኑ ሰዎች የእግዚአብሔር መቅደስ የሆነ ሰውነታቸው በቅድስናና በክብር ምስጋና የተጌጠ ነው፡፡
ሃይማኖትና ምግባር እንደነፍስና ሥጋ የተዋሃዱ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ነፍስ እንዳለው የሚታወቀው የሚታይ የሚዳሰስ ሥጋውን ስታንቀሳቅሰው ነው፡፡ እርሷ ባትታይም በሥራዋ ሀልዎቷ ይታወቃል፡፡ ሃይማኖትም የሚታይ የሚጨበጥ አይደለም፡፡ ሃይማኖት የሚታይ የሚዳሰሰው በምግባር ግዘፍ ሲነሣ ነው፡፡ ፆም ደግሞ የትሩፋት መግቢያ በር ነው፡፡ የአንዲት ሃይማኖት ተከታይ የሆነም በራሱ ፍልስፍና መጓዝ አይገባውም፡፡ ይልቁን የቤተክርስቲያኒቱን ቀኖና በመጠበቅና በመፈፀም ሃይማኖቱን በምግባር ይገልፃል እንጂ ፡፡ ያዕ 2፥14-26
የሚነበበው ወንጌል ማቴ፮፥፮-፳፬
ምንባቡን አንዱት ኃይለ ቃልን ማዕከል አድርገን እንመልከተው፡፡
-እንግድህ በአንተ ያለው ብርሃን ጨለማ ከሆነ ጨለማው እንዴት ይበረታ፡- ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ኃይለ ቃል እንደ ማሠሪያ ነው የተጠቀመው፡፡ በዚህ ምዕራፍ ለነፍስ ብርሃንነት የሚጠቅሙ ዋና ነገሮችን አስተምሯል፤፤ ምፅዋት ፆምና ጸሎት ዛሬ ስለሆዳቸው አብዝተው በሚጨነቁ ሰዎች እንደሚነሣው ፆም ያስፍጋል አያስፈልግም? መቼ እንፁም? ከምን እንፁም? ወዘተ… ዓይነት ጥያቄዎችን በጌታ ጊዜ አልተንሡም፡፡
ጸሎት ምፅዋት አስፈላጊነታቸው እንደማያጠያይቅ ሁሉ ፆምም አስፈላጊነቱ የተረጋገጠ ስለሆነ በምን ዓይነት መንፈሣዊ ይዘት መፆም እንዳለብን ብቻ ነው መመሪያ የተሠጠን፡፡
ፆምን ስንፆም ሁለት መሠረታዊ ነገሮችን እንድናሟላ ተነግሮናል፡፡
፩. ለታይታ እንዳናደርገው፡፡ ሰው ጦመኛ መሆናችን ቢያውቅ ከማድነቅ ባለፈ ዋጋ አይሠጠንም የጦማችንን መስዋዕት በረሃብ እሳት ተቀብሎ ዋጋ የሚሠጠን በስውር የሚያየን የሰማይ አባታቸን ብቻ ነው፡፡ ለሚጦሙ ለሚፀልዩና ምፅዋትን ለሚወዱ ሰዎች ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በተደጋጋሚ የሰማይ አባታችሁ ዋጋችሁን በግልጥ ይከፍላችኋል በማለት ከቅዱስ እግዚአብሔር ጋር ያለቸውን ሕብረት አረጋግጧል፡፡ ጦምን የሚነቅፉ ህብረታቸው ከማን ጋር ይሆን? እኒህን ድንጋይ ዳቦ እንዲሆኑ በል ከሚል ጋር ወይስ ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም በማለት ድል ከነሣ ጋር?
፪.በጦማችን ወቅት ለሌሎች መራራትን ስንጦም ለምግባችን ይውል የነበረውን ገንዘብ በከርሠ ነዳያን ውስጥ ከማኖር ይልቅ የጦሙ ወራት ሲያልቅ ለመጠቀም በሚል ብናኖረው ጦማችን ረብ ጥቅም አይኖረውም፡፡ እኛ ወደን ፈቅደን ከምግበ ሥጋ ስንከለከል ሳይወዱ በምግብ እጦት የሚጨነቁትን ማሰብ የክርስትና ግዴታ ነው፡፡
ሰውነታችን ከምግብ ሊከለል ነፍሳችን ከስስት፣ከፍቅረ ነዋይ፣ከጭካኔ፣ከትዕቢት ወዘተ…ካልጦመች እየተገዛን ያለነው ለገንዘብ(በቁሙ) እና በገንዘብ ተገዝቶ ሆድን ለሚሞላ ምግብ እንጂ ለእግዚአብሔር አይሆንም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት እንደማይቻል በፆምና ለስስት፣ለምፅዋትና ለፍቅረነዋይ፣ለትህትናና ለትዕቢት ወዘተ…ባንዴ ማደር አይቻልም፡፡
ይህን ከመከረ በኋላ ጌታችን ዓይን የሰውነት ብርሃን መሆኗን፤ዓይን ታማሚ ከሆነች ሰውነት ሁሉ እንደሚጨልም አይነተኛ ምሳሌ ከተናገረ በኋላ፤የሰውነት ብርሃን የምትሆን ነፍስም በመስገብገብ በግብዝነት በሀኬተኛነት ጉድፍ ከተበላሸች የከፋ ጨላማ እንደሚሆንብን አስጠንቅቋል፡፡ ነፍስ ብሩህ የምትሆነው ጦምን ጸሎትን ምፅዋትን ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ተዘክሮተ ሞትን አፅንታ ስትይዝ ነው፡፡ ነፍስ በቅድስና ብርሃን ካጌጠች የነፍስ ለሥጋ የሥጋ ቅድስና በአፍአ ላለው ሁሉ ይተርፋል፡፡ ያ ካልሆነ ግን የህይወታችን ብርሃን ይጨልማል፡፡ ለሥጋ ብርሃን ሕይወት የምትሆነው ነፍስ እንደሆነች፤ለነፍስ ብርሃኗ ሕይወቷ ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡ ሥጋ ነፍስ ስትለየው ይሞታል፡ነፍስ ደግሞ ጌታ እግዚአብሔር ሲለያት ትሞታለች፡፡