Login
Main menu

መሻገር

Index

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን !

 

የጳጉሜን ወር ከኖርንበት ለመኖር ተስፋ ወደ ምናደርግበት፤ ከሸኘነው ያለፈ ዓመት ወደ ምንቀበለው አዲስ ዓመት መሻገሪያ ናት፡፡ በባህላችንም በአዲስ ዓመት መባቻ ስንገናኝ የምንለዋወጠው መልካም ቃል ‹‹እንኳንከዘመንዘመንአሸጋገረን››   የሚል ነው ለመሆኑ ከዘመን ወደ ዘመን መሻገር ማለት ምን ማለት ነው? አንድ ሰው ወደ አዲስ ዘመን ተሻገረ የምንለው እንዴት ነው? ወይስ ከዘመን ዘመን መሻገር ማለት ለዘመናት መቁጠሪያነት ጌታ እግዚአብሔር በጠፈር ላይ ያኖራቸውን ዐውደ ፀሐይ፣ ዐውደ ወርኅ እና ዐውደ ከዋክብት ተጠቅመን የቀመርነውን የቀን አቆጣጠር አንድ ዐውድ ጨርሰን ሌላውን መጀመር ነው? 

 

ጌታ እግዚአብሔር ፍጥረታትን በጊዜ እየሠፈረ የፈጠረበት ምክንያት ፊት ያልነበሩ ኋላም ኃላፊ መሆናቸውን ሲያመለክተን ነው፡፡ ፍጥረታትን የሚሰፍር ጊዜ ባይኖር ኖሮ ሁሉ በቅድምና ነበረ ኋላም አያልፍም ለማለት የተመቸ ይሆን ነበር፡፡ ስለሆነም ፍጥረት መለወጥ ማርጀት እንዳለበት ለማጠየቅ ይህን ሂደት የሚሰፍርና የሚያሳውቅ መለኪያ ተሠራለት፡፡ በተጨማሪም ፍጥረታት በጊዜ ውስጥ መገኘታቸው፣ መኖራቸውና ኋላም ማለፋቸው ሠራዒ መጋቢ እንዳላቸው  በማመልከት ፍጥረት ሀለወተ እግዚአብሔርን ጮኾ እንዲመሠክር ያስገድዳል፡፡ ሥሉስ ቅዱስ ግን በባህርያቸው ውላጤ በዘመናቸው ብልየት የለበትምና ጊዜ ይሰፍረው ዘንድ አይችልም፡፡ ነቢዩ ዳዊት “አቤቱ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትህ፤ ሰማያትም የእጅህ ሥራ ናቸው፡፡ እነርሱ ይጠፋሉ፤ አንተ ግን ትኖራለህ፤ ሁላቸው እንደ ልብስ ያረጃሉ እንደ መጎናጸፊያም ትለውጣቸዋለህ፤ ይለወጡማል፡፡ አንተ ግን ያው አንተ ነህ፤ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም” እንዳለ፡፡ መዝ 101(102)፡ 25-27

 

በመሆኑም ከጌታ እግዚአብሔር ለፍጥረት የተቸረ የመጀመሪያ ሥጦታ ጊዜ መሆኑ የጊዜን ክብር የሚያሳይና የሰጪውንም ፍፁም ሥልጣን የሚገልጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ጊዜን እንደ ሰጠ የመንሳት ሥልጣንም የእርሱ ነውና፡፡ ኢሳ 38፡1-5 ፤ዳን 2፡21፤ የሐዋ.ሥራ 1፡7 ጌታ እግዚአብሔር ጊዜ የማይወስነው የፈቀደውን ለማከናወንም የጊዜ መስፈሪያነት የማያስፈልገው ቢሆንም ሥራውን(ልደተ ፍጥረትን) በጊዜ ውስጥ በማከናወን ጊዜ የተሰጠን ለሥራ መሆኑን አሳይቷል፡፡ ጊዜ የማይወስነው በጊዜ ውስጥ ከሠራ ጊዜ የሚወስነንማ እንግዲያው እንደምን ልንጠቀምበት ይገባ? ዘፍ 1፡1

 

ጌታ እግዚአብሔር ጊዜን ምሳሌ በማድረግ የፍጥረትን ህልውና ሂደትና ግብ አሳይቶናል፡፡ በመጀመሪያ ጊዜንና በጊዜ ውስጥ ፍጥረትን በማምጣት ካለ መኖር ወደ መኖር፤ ካለ መታወቅ ወደ መታወቅ ዘመን አሻገረን፡፡ በዚህም ከጊዜ በፊት የነበረው ዘመን የማይቆጠርለት ጥንቱ በዚህ ጊዜ ነው ተብሎ በዘመን የማይሰፈረው ዘመንን የሚሰፍረው ለመኖሪያ ዓለም (space) የማያስፈልገው ራሱን ዓለም አድርጎ የሚኖር እርሱ የነበረበት ነው፡፡ ከዚያ “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ” በማለት የጊዜና የፍጥረት ልደት በአንዲት ቅጽበት ተበሠረ፡፡ ጊዜ ፍጥረትን ፍጥረትም ጊዜን ሳይቀድም ተገኙ፡፡ ኗሪና መኖሪያው፤ ተሰፋሪና መሥፈሪያው፤ ተቆጣሪና መቁጠሪያው በአንዲት ቅጽበት ተገኙ፡፡ ከዚያ አንስቶ ጊዜ ለፍጥረት መሥሪያ ሆኖ እያገለገለ ፍጥረትም በጊዜ ውስጥ እየሰራ ወደ ፍጻሜያቸው ይጓዛሉ፡፡ በመጨረሻም በአንድ ተጠቅልለው ፍጥረትም ጊዜም ያልፋሉ፡፡ ጊዜ ያለ ፍጥረት ፍጥረትም ያለ ጊዜ አልነበረም አይኖርምም፡፡

ያም ሆኖ ግን ከፍጥረታት መካከል በጊዜ ውስጥ እንደሚኖር የሚያውቅ(time concsuessness) ያለው ሰው ብቻ ነው፡፡

 

ከዚህ የመሥሪያ ጊዜ ቀጥሎ የምንሻገር በጊዜ ወደማይሰፈር የዕረፍት ዘመን ነው፡፡ ይህ ዘመን እምነት በጥርጣሬ፣ ዕውቀት በድንቁርና የማይፈተኑበት መበላለጥ፣ መቀዳደም፣ የሌለበት ሁሉ በትምህርት ሳይሆን በባህሪያዊ ዕውቀት ወደ ፈጣሪው የሚቀርብበት ዘመን ነው፡፡ በሌላ አገላለጥ የመጀመሪያው ዘመን እንደታወቅን የማናውቅበት፤ ሁለተኛው ዘመን መታወቃችንን በማመን በመጠራጠርና በመካድ ውስጥ የምንዋልልበት፤ ሦስተኛው ዘመን ደግሞ ንዴተ ህላዌ ፈጽሞ ጠፍቶልን እንደታወቅን የምናውቅበት ዘመን ነው፡፡ ቆሮ 13 ይህ በመለኮታዊው ዕቅድ ፍጥረት የሚያልፍበት የዘመን ሽግግር ነው፡፡ አሁን ባለንበት የመሥሪያ ዘመን ባጋጠመን መታለል ልንሆን የሚገባንን ለመሆን ስላልቻልን ይኸኛውም ዘመን ለሁለት ተከፍለ፡፡ የድንቁርና፣ የድካም፣ የጉስቁልና፣ የልቅሶ የጩኸት የፍዳ ንዑስ ዘመን እና የዕውቀት፣ የኃይል፣ የተሐድሶ፣ የምስጋና፣ የምህረት ንዑስ ዘመን ሆነ፡፡ ይህንንም ማድረግ የቻለ የዘመናት ባለቤት የሆነ እርሱ በሥጋ ልደት የዘመን አካፋይ ሆኖ በመገለጥ ከአንዱ ዘመን ወደ ሌላው አሻገረን፡፡ የምህረት ዘመን ነው ስንል ግን አዋጅ በአዋጅ መለወጡ ለማጠየቅ እንጂ የሥራ(የተጋድሎ) ዘመን አብቅቷል ማለት አይደለም፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች” ቀን በማለት የአሁኑን የተጋድሎ ዘመን ፤ በሌሊት መስሎ ደግሞ የሚቀጥለው(ከሞት በኋላ) ሃይማኖት አጽንቼ የትሩፋት ሥራ ሠርቼ ዋጋ አገኛለሁ የማይባልባትን ዘመን አመልክቶናል፡፡ ዮሐ 9፡4   

 

በዚህ መሠረት ከዓመት ዓመት ስንሸጋገር ልብ ልንለው የሚገባ ዐቢይ ነጥብ ቢኖር ባለፈው ዓመት ምን ሠራሁ? በሚመጣውስ ምን ልሠራ ይገባኛል? የሚለውን ነው፡፡ ባለፈው ካልሠራን፤ ለሚመጣውም የኅሊና ዝግጁነትና ትንሳኤ ከሌለን ዘመን አልተሻገርንም፡፡ መሻገር ውስጥ ምን ጊዜም ለውጥ አለ፡፡ የሚታይ፣ የሚወራለት፣ የሚመሰከርለት፣ በቀጣይ ዘመን ውስጥ ሀልዎት እንዲኖረን የሚያስችል(የሚያበቃ) ሂደት አለ፡፡ በአጭሩ አንድ ሰው በተሰጠው ጊዜ ውስጥ ሥራ ካልሠራ አልኖረም( ህልውና አልነበረውም) ማለት ነው፡፡ በጊዜ ውስጥ ለመሥራት ወይም ላለመሥራት ሥልጣን ተሠጥቶት የተፈጠረ ሰው ብቻ ነው፡፡ ተጠየቅ ያለበትም ለዚህ ነው፡፡ ሌላው ፍጥረት ሁሉ የተገኘበትን ምክንያት በሥርዓተ ተፈጥሮ ፈጽሞ ያልፋል፡፡ ይህን የሚያደርጉ በፈቃድ ሳይሆን በቅድመ ውሳኔ ስለሆነ ምስጋናም ሆነ ወቀሳ የለባቸውም፡፡ ሰው ግን ይለያል፡፡ ምክንያተ ሀልዎቱን ዘንግቶ ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅና፣ ዐውደ ዓመትን በመቁጠር ብቻ ተወስኖ ከኖረ በቁሙ ሳለ ቁጥሩ ከሙታን ነው፡፡ ሙታናቸውን  እንዲቀብሩ ሙታንን ተውአቸው እንዳለ መጽሐፉ፡፡

 

በመሆኑም አንድ ሰው ከዓመት ዓመት፣ ከወር ወር፣  ከሳምንት ሳምንት፣ ከቀን ወደ ቀን ተሸጋገረ የምንለው ምክንያተ ተፈጥሮውን አክብሮ ወደ ቀጣዩ የፍጥረት ዐቢይ ዘመን የሚያሻግረውን የተወደደ ሥራ ሲሠራ፤ በሕይወቱ ላይ ለውጥ ታይቶ ለሌሎችም የለውጥ ምክንያት ሲሆን ነው፡፡ ምክንያተ ፍጥረቱን ዘንግቶ ከፈጣሪው ተለይቶ ከፍጥረተ ዓለም ተጣልቶ የምድርን ጸጋ እንደ ተምች በልቶ ለኖረባትና የሰው ዘር ለሚቀጥልባት የአዳም ማኅጸን ምንም ሳያበረክት፤ እየኖረ እንደሆነ የሚያስብ ከሆነ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ንግግር ከሰውነት ደረጃ ወርዶ የምግብ ማመላለሻ ቱቦ ሆኗል ማለት ነው፡፡

 


Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ