“መንሹ በእጁ ነው፤ ...... "
Index
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!
“መንሹ በእጁ ነው፤ አውድማውን ያጠራዋል” ማቴ 3:12
በምህረቱ ባለጠጋ የሆነ ጌታ እግዚአብሔር የመጨረሻውን ፍርዱን ከመግለጡ በፊት የንስሐ ዕድል መስጠት ልማዱ ነው፡፡ ይህንን እውነታ ከኖኅና ከሰዶም ሰዎች ገጠመኝ ከነነዌም ታሪክ በግልጽ ማየት ይቻላል፡፡ የተመለሱ ድነዋል፤ በልባቸው ጥንካሬ ጸንተው በክፋት የቀጠሉ ጠፍተዋል፡፡ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ከላይ የተጠቀሱትን ታሪኮች እንደማሳያ ተጠቅሞባቸዋል፡፡ የሰማው የለም እንጂ፡፡ ማቴ 12፡41፤ ማቴ 24፡38፤ ሉቃ 17፡28-32
አውድማውን ያጠራ ዘንድ መንሹን የያዘው ከመገለጡ በፊት ቤተ አይሁድ በክፋት ላይ ክፋት እየጨመሩ ሄደው ነበር፡፡ ዕለት ተዕለት ጌታ እግዚአብሔርን በከንፈራቸው ምህረትንና በረከትን በሥራቸው ግን ፍርድንና ጥፋትን እየለመኑት ነበር፡፡ ሁሉን ቻይ የሆነው እርሱ ግን አባቱን በግፍ ያስገደሉበትን ብላቴና ለበቀል ሳይሆን ወደ ምህረት ጮኾ እንዲጠራቸው ላከው፡፡ በምድረ በዳ (አበው በትርጓሜ ምድረ በዳ የተባለ የአይሁድ ልቡን ነው፡፡ ምድረ በዳ ውሃ ልምላሜ እንደሌለበት የአይሁድ ልቡናም ከሃይማኖት ከምግባር የተራቆተ ነበር ይላሉ፡፡ ስም፣ ሥርዓትና ምልክት ብቻ ቀርቶላቸው ነበር፡፡ ዛሬም በእኛ ዘንድ ያለው ክርስትና ስም፣ ሥርዓትና ምልክት ብቻ ቀርቶልን በፍቅር ከሆን ሃይማኖትና ምግባር ጠፍ ሆነናል) የተገለጠው ሰባኪም በትምህርቱ የነበሩበትን ሁኔታ ገልጦ አሳያቸው፡፡ ትምህርት መስታወት ነው፡፡ መስታወት ፊታችን ላይ ያለብንን አደፍ ጉድፍ ገልጦ ቢያሳይ እንጂ እንዳያፀዳ ትምህርትም በራሱ ድኅነት አያመጣም፤ ነውርን ገልጦ ያሳያል እንጂ፡፡ ሰምቶ መመለስ ለእያንዳንዱ የተተወ ምርጫ ነው፡፡ ትምህርቱም በሦስቱ መደብ ተለይቶ የቀረበ ነበር፡፡ ለቤተ ክህነቱ፣ በመንግሥት አስተዳደር ለነበሩና ለሕዝቡ፡፡
ከሕዝቡ እንጀምርና በደረጃ ወደ ላይ እየወጣን ለመመልከት እንሞክር፡፡ ሕዝቡ የዮሐንስን ትምህርት ሰምተው ምን እናድርግ? ሲሉ የመከራቸው “ሁለት ልብስ ያለው አንዱን ለሌለው ይስጥ፤ ምግብም ያለው እንዲሁ ያካፍል” በማለት ነው፡፡ በዚህ ንግግሩ ሕዝቡ የነበረበትን ሁኔታ ገልጾታል፡፡ ሰው ከመረዳዳትና ከመተዛዘን ይልቅ ሁሉ በግለኝነት መንፈስ የሰከረበት፤ ሀብት በማከማቸት የታወረበት፤ ለወገን መራራት እንደ ሞኝነት የተቆጠረበት፤ ተካፍሎ መብላት በነበር የቀረበት፤ በልጦ መታየትና በወንድም ላይ መኩራት መለያ የሆነበት ዘመነ እኪት ነበር፡፡ ቤተ አይሁድ የኖሩበት የአባቶቻቸው ባህል ይኸውም መተዛዘን፣ መረዳዳት፣ መተባበር ከመካከላቸው ጠፍቶ በምትኩ በተደጋጋሚ በባርነት የገዟቸው የአህዛብ ልማድ አማሰናቸው፡
፡ በይበልጥ የሄለናውያን(Helenistic) የአመለካከትና የአኗኗር ዘይቤ ከፍተኛ ተጽዕኖ የማንነት ግራ መጋባት ትግል ውስጥ ዘፈቃቸው፡፡ የጥንቱን የአይሁድ ባህል እንዳይጠፋ በሚቀኑና በአዲሱ ልማደ አህዛብ በተጠመቁ መካከል ልዩነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ ይሰፋ ነበር፡፡ ይህም በአንድ አሳብ ተስማምቶና ተረዳድቶ ከመኖር ይልቅ በልዩነት ለመነታረክ ምክንያት ሆነ፡፡ እንኳን በጠላቶቻቸው ላይ ድል ሊያገኙ ቀርቶ እርስ በርሳቸው በጠላትነት አንዱ በሌላው ላይ ተነሱ፡፡ ዛሬ በእኛም የሚታይ ቤተ አይሁድ ጥፋታቸው በቀረበበት ጊዜ ያሳዩ የነበረው ጠባይ ነው፡፡ ቀድሞ እንታወቅባቸው የነበሩ አባቶቻችን በሰላምና በበረከት እንዲኖሩ ያስቻሏቸው አብሮ በመተሳሰብና በመተዛዘን መኖር ከእኛ ርቋል፡፡ ከስግብግብነታችን ብዛት አማራጭ በማይቀርብላቸው የጤናና የትምህርት ጉዳይ ላይ እንኳ ወገናችንን እንዘርፋለን፡፡ በሰው ጤናና ነገ ሀገር በሚረከቡ ሕጻናት ሕይወት ላይ ከመነገድ የከፋ ኅሊና ቢስነትና የሥነ ምግባር ዝቅጠት የለም፡፡ ኢትዮጵያውያን አሁን ባለንበት ማንነት ዓይናችንን ቀና አድርገን ከጌታ እግዚአብሔር ዘንድ ምህረትንና በበረከት የተሞሉ ዘመናትን ለመለመን የሚያበቃ የሞራል ብቃት የለንም፡
፡ ምህረት የሚሰጠው በራሳቸው ላይ ሊደረግባቸው የማይወዱትን በሌላው ላይ ለማያደርጉና ምህረት ለተገባቸው ነው፡፡ ለግፈኛ ምህረት ማድረግ በክፉ ሥራህ ግፋበት እንደማለት ነው፡፡ አሁን የሚያድነን ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት ወዘተ .
. . አይደለም፤ ግፍ መሥራትን ማቆም እንጂ፡፡ ግፍ እየሠሩ ጾምና ጸሎት በጌታ እግዚአብሔር ላይ መዘበት ነው፡፡
በሀገር አስተዳደር ረገድ ደግሞ የሮም መንግሥት ሕግንና የሠለጠነ የአስተዳደር ዘይቤን ሽፋን በማድረግ ብዙ ግፍ ይፈፅም ነበር፡፡ ዛሬ ብዙ በኢኮኖሚ ራሳቸውን ያልቻሉ የዓለም ሀገራትን በዲሞክራሲና በሰብዐዊ መብት ሽፋን ሴራን እየደበቁ የማድቀቅና የማንነት ክስረት ውስጥ የመክተት አካሄድ ዛሬ የመጣ ሳይሆን ከቀድሞ የተወረሰ ነው፡፡ ዛሬም እኛ በግልፅና በሥውር ማን እንደሚገዛን የታወቀ ነው፡፡ ዛሬ ያሉ መንግሥታት ታላላቅ ግፍ የሚፈጽሙ የሕገ መንግሥትን፣ የዲሞክራሲንና የሰብዓዊ መብቶችን ድንጋጌ ጭምብል አጥልቀው ነው፡፡ እንዲህ ያሉትን ክቡር ዳዊት በመንፈሰ ትንቢት ተመርቶ እንዲህ ገልጿቸዋል፡፡
ሰነፍ በልቡ አምላክ የለም ይላል፤
በሥራቸው ረከሱ ጎሰቆሉ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ የሚያስተውል እግዚአብሔርንም የሚፈልግ እንዳለ ያይ ዘንድ፤