Login
Main menu

እስረኞቹ

Index

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን!

በተኛበት የዋሻ እስር ቤት ቅዝቃዜ ሰውነቱ ደንዝዟል ለእርሱ ብቻ በሚሰማው ቃል ግን መንፈሱ ግሏል፡፡ አካሉ በደረሰበት እንግልት ደቋል ልቡ ግን እንደ ዓለት ፀንቷል፡፡ የመንፈስ ልጆቹ ዓይን ውስጥ ያየው አንተ ከሌለህ ምን እንሆናለን? የሚለው ጭንቀት የማያንቀላፋ እረኛ የራሳቸውን ፀጉር እንኳ ቆጥሮ የሚያውቅ ጠባቂ እንዳላቸው ካለመረዳት የመጣ እንደሆነ በመረዳቱ የፀናውን እውነት እንደሚገባው አልገለጥኩላቸው ይሆን? ሲል ላፍታ አሰበ፡፡ ከተቀመጠበት በውኃ የላቆጠ የእስር ቤት ወለል ላይ ተነስቶ የእስር ቤቱን ዘብ ለልጆቹ መልዕክት የሚጽፍበት ብዕርና ክርታስ እንዲሰጠው በትኁት ድምጽ ለመነው፡፡ በጭካኔ የደደረው የሮማ ወታደር ልብ በማያውቀው ምክንያት በእስረኛው ላይ መጨከን ተሳነው፡፡ ትንሽ እልፍ ብሎ ከተቀመጠው ጠረጴዛ ላይ ብዕርና ክርታሱን እንዲሁም ቁራሽ ዳቦ አቀበለው፡፡ ኅብስቱን እንደ ተቀበለ እጆቹ እየተንቀጠቀጡ እንባ ባቀረሩ ዓይኖቹ ዘቡን ተመለከተው፡፡ ዘቡ ምን የሚያስከፋ ነገር እንዳደረገ በመደናገር ትኩር ብሎ እስረኛውን ሲያጠናው በዕድሜና በእንግልት ከደከመ ልሳን የሚያስደንቅ ጥንካሬ ያለው ቃል መፍለቅ ጀመረ፡፡ 

 

እኛ አስራ ሁለታችን፣ እናቱና ከገሊላ ጀምሮ የተከተሉት ሴቶች አብረን አጠገቡ ጉብታው ላይ ተቀምጠናል ሕዝቡ ግን ታቹን ሜዳውን ሞልቶታል፤ በግምት የአምስት ገበያ ሕዝብ ይሆናል፡፡ ከፊልጶስና ከእንድርያስ ጋር ጥቂት ቃላት ከተነጋገሩ በኋላ “ይበቃል” ሲላቸውና እርስ በርስ ግራ በመጋባት ሲተያዩ ተመለከትኳቸው፡፡ ወዲያው ጌታችን ፊልጶስ አጠገቡ በዕንቅብ ያስቀመጠውን አምስት ኅብስትና ሁለት ዓሣ ይዞ አሻቅቦ ወደ ሰማይ ዐየና ባረከ፤ ቆርሶም ለሁላችን ሰጠን፤ እኛም ለሌላው እንዲሁ፡፡ የሆነው ሁሉ ልንገነዘበው ከምንችለው በላይ ስለ ሆነብን የጎረስነውን እንኳ መዋጥ አቅቶን ሁላችን ዓይን ዓይኑን በማየት ደንዝዘን ቆምን፡፡ ሕዝቡ በታላቅ ደስታና መደነቅ ተይዞ ከበረከቱ ይሳተፋል፡፡ በዚያ ጫጫታ መካከል “ከሰማይ የወረደ እውነተኛ የሕይወት ኅብስት እኔ ነኝ፤ የሰውን ልጅ ሥጋውን ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፡፡ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ ግን የዘላለም ሕይወት አለው፤ ከሞት ወደ ሕይወት ተሸጋገረ እንጂ ሞትን አያይም” ብሎ በመንፈሱ ቃተተ፡፡ የሚነግረን ቃል ሕይወትና መንፈስ ስለነበር እንዳልገባን ተረድቶናል፡፡ ቃሉን ለመረዳት በራሱ ከላይ ኃይል ያስፈልጋል፡፡ ለካስ ለዚያ ኖሯል በሌላ ጊዜ “ብዙ የምነግራችሁ ነገር ነበረኝ ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ግን ሁሉን ያስታውቃችኋል” ያለን፡፡

 

ተላልፎ በተሰጠባት በዚያች ሌሊትም በመካከላችን ቆሞ ኅብስቱን አነስቶ ባረከ “እንካችሁ ይህ ሥጋዬ ነው ሁላችሁ ከእርሱ ብሉ፣ ደግሞም ወይኑን አንስቶ አመሰገነ ሁላችሁ ከዚህ ጠጡ ይህ ስለ እናንተ የሚፈስ ደሜ ነው ሁላችሁ ከእርሱ ጠጡ፤ ይህን በምታደርጉ ጊዜም ሞቴንና ትንሣኤዬን ታስባላችሁ” አለን፡፡ አሁንም አንተ ኅብስቱን ስትሠጠኝ ከእርሱ ጋር የነበረኝ ጊዜ ትዝ ስላለኝ ነው እንጂ ያንተ በጎነት እንከን ኖሮበት ስላይደለ ቅር አትሰኝ አለው እስረኛው፡፡ የእስረኞቹ ዘብ በሰማው ተደንቆ “እንዲህ በእያንዳንዷ የሀሳብ ልውውጥና ድርጊት ልታስቡት፣ በፍቅሩ ልትቃጠሉና በናፍቆቱ ልትንገበገቡ የቻላችሁ ምን ዓይነት ጌታ ቢሆን ነው? በእያንዳንዱ የኑሮ ሂደት እርሱን እያሰባችሁ በሲቃ መሞላትስ ሕመምና ድካም አይሆንባችሁም? ሕይወታችሁንስ በትካዜ የተሞላ አያደርገውም?” ሲል በመደነቅ እስረኛውን ጠየቀው፡፡ ይህን ሁሉ ለማብራራት ጊዜ ያጥርብኛል፡፡ ይህን ለመረዳት ከእርሱ ጋር ሰው ዓየር ስቦ የሚያስወጣበትን ያህል ቅፅበት ቢኖርህ እመኝ ነበር፡፡ ምሥጢሩ ግን እርሱን በማወቅ፤ ሕይወትና ደስታ የሚለውንም ሐሳብ በምትተረጉምበት መንገድ ይፈታል፡፡ ስሜት ከቃላት በላይ ነው፡፡ ስሜትን መኖር እንጂ ለሌሎች ማጋራት እጅግ ከባድ ነው፤ በውስጡ ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ ለማንኛውም አንተ ይቺን የመጨረሻ ኑዛዜዬን ለልጆቼ ልታደርስልኝ ፈቃድህ ከሆነና እኛ የምንኖረውን ለመኖር ድፍረቱ ካለህ እኛ የቀመስነውን መቅመስ ትችላለህ፡፡ ስለ እኛ ግን በአጭሩ ለማስረዳት በክርስቶስ ወንድማችን የሆነ ጳውሎስ የጻፈውን ላሰማህ፡፡ እንዲህ ይላል “ ነገር ግን በሁሉ እንደ እግዚአብሔር አገልጋዮች ራሳችንን እናማጥናለን፤ በብዙ መጽናት፣ በመከራ፣ በችግር፣ በጭንቀት፣ በመገረፍ፣ በወኅኒ፣ በሁከት፣ በድካም፣ እንቅልፍ በማጣት፣ በመጦም፣ በንጽህና፣ በእውቀት፣ በትዕግስት፣ በቸርነት፣ በመንፈስ ቅዱስ፣ ግብዝነት በሌለው ፍቅር፣ በእውነት ቃል፣ በእግዚአብሔር ኃይል፣ ለቀኝና ለግራ በሚሆን በጽድቅ የጦር ዕቃ፣ በክብርና በውርደት፣ በክፉ ወሬና በመልካም ወሬ ራሳችንን እናማጥናለን፡፡ አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን፤ ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን፤ የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን፤ የተቀጣን ስንሆን አንገደልም፤ ኀዘንተኞች ስንሆን ዘወት ደስ ይለናል፤ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለ ጠጎች እንደርጋለን፤ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው ” ፡፡ በሌላ ሥፍራም “ በሁሉ እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤ እናመነታለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም፤ እንሰደዳለን እንጂ አንጣልም፤ እንወድቃለን እንጂ አንጠፋም፡፡ የኢየሱስ ሕይወት ደግሞ በሥጋችን ይገለጥ ዘንድ ሁልጊዜ የኢየሱስን መሞት በሥጋችን ተሸክመን እንዞራለን፡፡ የኢየሱስም ሕይወት ደግሞ በሚሞት ሥጋችን ይገለጥ ዘንድ እኛ ሕያዋን የሆንን ከኢየሱስ የተነሳ ዘወትር ለሞት አልፈን እንሰጣለን፡፡ . . . ስለዚህም አንታክትም! ነገር ግን የውጪው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል፡፡ የማይታየውን እንጂ የሚታየውን ባንመለከት ቀላል የሆነ የጊዜው መከራችን የክብርን የዘላለም ብዛት ከሁሉ መጠን ይልቅ ያደርግልናልና የሚታየው የጊዜው ነውና የማይታየው ግን የዘላለም ነው” ይላል፡፡ ወንድሜ ሆይ አሁን ፍቀድልኝና ኑዛዜዬን ልጻፍ ከዚያ ፈቃድህ ከሆነ ብርሃንን ታያለህ ብሎ እስረኛው ወደ ሥፍራው ተመለሰ፡፡ የእስረኞቹ ዘብ ፈዞ እየተመለከተ እስረኛው የተቀበለውን ኅብስት በዕድሜ ለጋና ቁጡ የሆነ ሁሉን ለሚያመናጭቅ በነፍስ መግደል ለታሠረ ሌላ እስረኛ ሠጠው፡፡ በለዘበ አንደበትም ገና ብዙ ሥራ ይጠብቅሀል፤ አትሞትም፡፡ ከዚህ ስትወጣ ግን የእግዚአብሔርን ቸርነትና እኔም የነገርኩህን አትርሳ፡፡ 


Leave a comment

Make sure you enter the (*) required information where indicated. HTML code is not allowed.

back to top

ጠቃሚ አድራሻዎች

መጻሕፍት ቢያነቧቸው

  • * ​ፍቅር 
  • ፍና ቅዱሳን
  • * የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱ እና ትምህርቱ 
  • * ዝጎራ